አሜሪካ ተኩስ ለማቆም ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥን እንድትከፍት ቅድመ ሁኔታ አቀረበች
አንድ ወር ያለፈው ጦርነት የሚቆምበት መንገድን በተመለከተ ከሁሉም ወገን የተለያየ እና የሚቃረን አስተያየት እየተሰነዘረ ባለበት በአሁኑ ጊዜ ጥቃቶች እና የአጸፋ ጥቃቱ ቀጥሏል።
ትራምፕ ጦርነቱ በጥቂት ሳምንታት ውስጥ እንደሚቆም መናገራቸውን ተከትሎ ኢራን ድርድር ለማድረግ ጥያቄ ማቅረቧን ከገለጹ ከሰዓታት በኋላ ከኢራን በኩል ተቃራኒ ዜና ወጥቷል።
የኢራን ቴሌቪዥን ዛሬ ከሰዓት በኋላ የአገሪቱን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይን ጠቅሶ እንደዘገበው ፕሬዝዳንት ትራምፕ ከኢራን በኩል የድርድር ጥያቄ ቀርቧል መባሉን “ሐሰት እና መሠረተ ቢስ” ነው መባሉን ሮይተርስ ዘግቧል።
አሜሪካ እና እስራኤል እያካሄዱት ባለው ጥቃት ኢራን ከባድ ውድመት ቢደርስባትም የአጸፋ ጥቃቷ በመካከለኛው ምሥራቅ አገራት ውስጥ ከባድ ፍርሃትን አስፍኗል።
በተጨማሪም ከፍተኛ መጠን ያለው የዓለም ነዳጅ የሚተለላፍበትን የሆርሙዝ ወሽመጥ በመዝጋቷ በአብዛኛው ዓለም ክፍል ውስጥ የነዳጅ እጥረት እና የዋጋ ንረት ተከስቷል።
በዚህም ምክንያት የጦርነቱ ቀስቃሾች አሜሪካ እና አስራኤል እየተወቀሱ ሲሆን፣ ኢራን የባሕር መተላለፊያውን ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ የምትከፍት ከሆነ አሜሪካ ተኩስ ለማቆም እንደምትስማማ እየተዘገበ ነው።
በተጨማሪም የአሜሪካ ምክትል ፕሬዝዳንት ጄዲ ቫንስ “በአሸማጋዮች” በኩል ከኢራን ጋር ንግግር እያደረጉ መሆናቸውን እና የሆርሙዝ ወሽመጥ መከፈት ላይ ኢራን የአሜሪካን ቅድመ ሁኔታን እንድትቀበል በምሥጢር መልዕክት እንደተላለፈላት ሮይተርስ ዘግቧል።
የአሜሪካ የዜና ድረ ገጽ የሆነው አክሲዮስ እንደዘገበው ተኩስ ለማቆም በምላሹ የሆርሙዝ መተላለፊያን ለማስከፈት ንግግር እየተካሄደ ነው።
ኢራን ግን ከተኩስ አቁም ይልቅ ዘላቂ ጦርነት የማቆም ዋስትና እዲሰጣት በመጠየቅ ሌሎችንም ቅድመ ሁኔታዎችን አስቀምጣለች።