ቀጥታ, አሜሪካ ተኩስ ለማቆም ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥን እንድትከፍት ቅድመ ሁኔታ አቀረበች

በበርካታ የዓለም አገራት ውስጥ የነዳጅ አቅርቦት እጥረት እና የዋጋ መናር ያስከተለው የሆርሙዝ ወሽመጥ መዘጋት ማብቃትን አሜሪካ ለተኩስ አቁም እንደ ቅድመ ሁኔታ አቅርባዋለች።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. አሜሪካ ተኩስ ለማቆም ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥን እንድትከፍት ቅድመ ሁኔታ አቀረበች

    አንድ ወር ያለፈው ጦርነት የሚቆምበት መንገድን በተመለከተ ከሁሉም ወገን የተለያየ እና የሚቃረን አስተያየት እየተሰነዘረ ባለበት በአሁኑ ጊዜ ጥቃቶች እና የአጸፋ ጥቃቱ ቀጥሏል።

    ትራምፕ ጦርነቱ በጥቂት ሳምንታት ውስጥ እንደሚቆም መናገራቸውን ተከትሎ ኢራን ድርድር ለማድረግ ጥያቄ ማቅረቧን ከገለጹ ከሰዓታት በኋላ ከኢራን በኩል ተቃራኒ ዜና ወጥቷል።

    የኢራን ቴሌቪዥን ዛሬ ከሰዓት በኋላ የአገሪቱን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይን ጠቅሶ እንደዘገበው ፕሬዝዳንት ትራምፕ ከኢራን በኩል የድርድር ጥያቄ ቀርቧል መባሉን “ሐሰት እና መሠረተ ቢስ” ነው መባሉን ሮይተርስ ዘግቧል።

    አሜሪካ እና እስራኤል እያካሄዱት ባለው ጥቃት ኢራን ከባድ ውድመት ቢደርስባትም የአጸፋ ጥቃቷ በመካከለኛው ምሥራቅ አገራት ውስጥ ከባድ ፍርሃትን አስፍኗል።

    በተጨማሪም ከፍተኛ መጠን ያለው የዓለም ነዳጅ የሚተለላፍበትን የሆርሙዝ ወሽመጥ በመዝጋቷ በአብዛኛው ዓለም ክፍል ውስጥ የነዳጅ እጥረት እና የዋጋ ንረት ተከስቷል።

    በዚህም ምክንያት የጦርነቱ ቀስቃሾች አሜሪካ እና አስራኤል እየተወቀሱ ሲሆን፣ ኢራን የባሕር መተላለፊያውን ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ የምትከፍት ከሆነ አሜሪካ ተኩስ ለማቆም እንደምትስማማ እየተዘገበ ነው።

    በተጨማሪም የአሜሪካ ምክትል ፕሬዝዳንት ጄዲ ቫንስ “በአሸማጋዮች” በኩል ከኢራን ጋር ንግግር እያደረጉ መሆናቸውን እና የሆርሙዝ ወሽመጥ መከፈት ላይ ኢራን የአሜሪካን ቅድመ ሁኔታን እንድትቀበል በምሥጢር መልዕክት እንደተላለፈላት ሮይተርስ ዘግቧል።

    የአሜሪካ የዜና ድረ ገጽ የሆነው አክሲዮስ እንደዘገበው ተኩስ ለማቆም በምላሹ የሆርሙዝ መተላለፊያን ለማስከፈት ንግግር እየተካሄደ ነው።

    ኢራን ግን ከተኩስ አቁም ይልቅ ዘላቂ ጦርነት የማቆም ዋስትና እዲሰጣት በመጠየቅ ሌሎችንም ቅድመ ሁኔታዎችን አስቀምጣለች።

  2. በቴህራን በሚገኝ የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ላይ ጥቃት ደረሰ

    በኢራን ዋና ከተማ ቴህራን ውስጥ ዛሬ በተፈጸመ ጥቃት የሩሲያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ሕንጻ ጉዳት እንደደረሰበት በአገሪቱ የሚገኘው የሩሲያ ኤምባሲ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጹ አስታወቀ።

    ኤምባሲው “ቴህራን በሚገኘው የቅዱስ ኒኮላስ የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን አቅራቢያ ሁለት ጊዜ ጥቃት ተፈጽሞ፣ የቤተ ክርስቲያኑ ዋና ሕንጻ የእንግዶች ማረፊያ እና ሌሎች ቁሳቁሶች ላይ ጉዳት ደርሷል” ብሏል።

    የሩሲያ ኤምባሲ ከፊል ጣሪያው የፈረሰ ሕንጻ እና የተሰባበሩ መስኮቶችን የሚያሳዩ ምሥሎችንም ከመልዕክቱ ጋር አብሮ አጋርቷል።

    በቤተ ክርስቲያኑ ላይ ጥቃቱ የተፈጸመው ለክርስቲያኖች ዋነኛ የሆነው የትንሳዔ በዓል እየተቃረበ ባለበት ጊዜ መሆኑ “የአሜሪካ እና የእስራኤል ወደታራዊ ጀብደኝነት በኢራን የሚገኙ የኦርቶዶክስ እምነት ተከታዮችን የሚሰባሰቡበትን ስፍራ አሳጥቷቸዋል” ሲል ኤምባሲው ወቅሷል።

    የቅዱስ ኒኮላስ ካቴድራል በሩሲያዊው የሥነ ሕንጻ ባለሙያ የተነደፈ ሲሆን፣ በኢራን ብሔራዊ የቅርሶች መዝገብ ውስጥ እንደ አገሪቱ ቅርስ ተመዝግቧል።

    የሩሲያ ኤምባሲ አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ እየፈጸሙት ያለው ጥቃት የሲቪል መሠረተ ልማቶችን፣ ባሕላዊ እና ሃይማኖታዊ ቅርሶች ዒላማ እያደረገ መሆኑን በመገልጽ አውግዞታል።

  3. ኢራን የተኩስ አቁም ጥያቄ ማቅረቧን ትራምፕ ተናገሩ

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ “የኢራን አዲስ አመራር ፕሬዝዳንት” የተኩስ አቁም ጥያቄ አቅርበዋል አሉ።

    ፕሬዝዳንቱ ትሩዝ ሶሻል በተባለው ማኅበራዊ ሚዲያቸው ላይ ባሰፈሩት ጽሑፍ “ይህ ሰው እምብዛም አክራሪ አይደለም። ከእሱ ቀደም ሥልጣን ላይ ከነበሩት በተሻለ አዋቂ ነው” ብለዋል።

    ይህንን የፕሬዝዳንት ትራምፕ አስተያየትን በተመለከተ አስካሁን ከኢራን በኩል የተሰጠ አስተያየት የለም።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ከዚህ ቀደም ኢራን ለድርር ጥያቄ አቅርባለች ብለው ቢናገሩም ከኢራን በኩል ግን ጥያቄ አለመቅረቡ በግልጽ ሲነገር ነበር።

    የኢራን ፕሬዝዳንት እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትርን ጨምሮ ከፍተኛ ባለሥልጣናት ጦርነቱ በተኩስ አቁም ሳይሆን ሙሉ ለሙሉ በዘላቂነት መቆም እንዳለበት ከስምምነት መደረስ እንዳላበት አሳውቀዋል።

    አሁንም ኢራን ከስምምነት የምትደርሰው ድጋሚ ጦርነት እንደማይከፈትባት ዋስትና ሲሰጣት ብቻ መሆኑን ቅድመ ሁኔታ አቅርባለች።

    ትራምፕ አክለውም “የሆርሙዝ ወሽመጥ ሲከፈት እና ነጻ ሲሆን የምናስብበት ይሆናል። እስከዚያ ድረስ ግን ኢራንን ወደ ምንምነት ለመለወጥ ማጋየታችንን እንቀጥላለን። ወደ ድንጋይ ዘመን እንመልሳታለን” በማለት ጽፈዋል።

    ትራምፕ አዲሱ የኢራን መሪ በማለት በተደጋሚ እያደነቋቸው ያሉት ፖለቲከኛ ማን እንደሆኑ ለማወቅ እዚህ ያንበቡ ከአሜሪካ ጋር ለሚደረገው ንግግር ቁልፍ ሰው እና ቀጣዩ መሪ ይሆናሉ የሚባሉት የኢራን አፈጉባኤ ማን ናቸው?

  4. ሥልጣን ከተረከቡ በኋላ በአደባባይ ያልታዩት የኢራን ጠቅላይ መሪ መልዕክት አስተላለፉ

    የአባታቸውን ሥልጣን ከተረከቡ በኋላ በአደባባይ ያልታዩት አዲሱ የኢራን ጠቅላይ መሪ ሞጅታባ ኻሜኒ፤ ለሄዝቦላህ መሪ ያላቸውን ድጋፍ በጽሑፍ ገለጹ።

    ጠቅላይ መሪው የሊባኖሱ ታጣቂ ቡድን ሄዝቦላህ መሪ ኒያም ቃሲምን እንደሚደግፉ በጽሑፋቸው አስፍረዋል።

    የቀድሞው ጠቅላይ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒ ግድያን ተከትሎ ሄዝቦላህ “ሐዘኑን መግለጹን” ጠቅሰውም ለቡድኑ ምስጋና አቅርበዋል።

    የሞጅትባ አባት የተገደሉት አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ ጥቃት በከፈቱበት የመጀመሪያው ቀን ነበር።

    አዲሱ ጠቅላይ መሪ አባታቸውን ከተኩበት ጊዜ አንስቶ ለሕዝብ አልታዩም።

    እስራኤል አዲሱን ጠቅላይ መሪ ዒላማ እንደምታደርግ በተደጋጋሚ ዝታለች።

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ደግሞ “ማንም አላየውም። ስለዚህ ወይ ሞቷል፤ ወይ ክፉኛ ተጎድቷል” ብለዋል።

    በመንግሥታቱ ድርጅት የኢራን አምባሳደር በበኩላቸው ጠቅላይ መሪው በአደባባይ ያልታዩት “ለደኅንነታቸው ሲባል ነው” ብለዋል።

  5. ኢራን ላይ እየተፈጸመ ባለው ጥቃት ከ130 በላይ ታሪካዊ ቅርሶች ጉዳት እንደደረሰባቸው ተነገረ

    አሜሪካ እና እስራኤል እየፈጸሙት ባለው ጥቃት ምክንያት ከ130 በላይ ታራካዊ ቅርሶች መውደማቸውን የኢራን መንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ።

    የኢራን ባሕላዊ ቅርሶች ሚኒስቴር መስክ ላይ ያደረገውን ቅኝት መሠረት በማድረግ በቀረበው ዘገባ ቁጥራቸው 132 የሚሆኑ ታሪካዊ ቅርሶች እና ጥንታዊ ሃውልቶች ጉዳት ደርሶባቸዋል።

    እየተካሄደ ባለው ጥቃት በኢራን ውስጥ በሚገኙ 18 ግዛቶች ውስጥ የሚገኙ ታሪካዊ ሃውልቶች እና ሕንጻዎች ጉዳት ደርሶባቸዋል ወይም ወድመዋል ብሏል ሚኒስቴሩ።

  6. የዩኬ ጠቅላይ ሚኒስትር በኢራን ጦርነት ላይ የያዙትን አቋም እንደማይቀይሩ ተናገሩ

    በኢራን ጦርነት የመሳተፍ ዕቅድ እንደሌላቸው ሲናገሩ የቆዩት የዩናይትድ ኪንግደም ጠቅላይ ሚኒስትር ኪር ስታርመር፤ “ምንም ጫጫታ” ቢኖር “አቋሜን አልቀይርም” አሉ።

    የዩናይትድ ኪንግደምን “የረጅም ጊዜ ብሔራዊ ጥቅም ማስጠበቅ ከአውሮፓ አጋሮች እና ከአውሮፓ ኅብረት ጋር የጠበቀ ግንኙነት መኖርን እንደሚጠይቅ”፤ “ይበልጥ ግልጽ” እየሆነ መምጣቱንም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ተናግረዋል።

    ስታርመር የኢራን ጦርነትን በተመለከተ ዛሬ ረቡዕ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፤ ከአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ጋር ግንኙነታቸው እየሻከረ በመሆኑ ከአውሮፓ ጋር ያላቸውን ትስስር እያጠበቁ እንደሆን ተጠይቀዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከአውሮፓ እና ከአሜሪካ እንደማይመርጡ በመግለጽ ምላሽ ሰጥተዋል። “ከአሜሪካ እና ከአውሮፓ ጋር ጠንካራ ግንኙነት እንዲኖረን ማድረግ ለእኛ ጠቃሚ ይመስለኛል” ብለዋል።

    “መከላከያ እና ደኅንነት፣ የኤነርጂ ልቀት እንዲሁም ኢኮኖሚን በተመለከተ ግን ከአውሮፓ ጋር ጠንካራ ግንኙነት ያስፈልገናል” ሲሉ ተናግረዋል። በአውሮፓ የሚደረግ ጠንካራ ትብብር ከአሜሪካ ጋር ያለ ግንኙነትንም እንደሚያግዝም አክለዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ስታርመር በኢራን ጦርነት ላለመሳተፍ በመወሰናቸው ከፍተኛ ጫና እንደደረሰባቸው በጋዜጣዊ መግለጫው ጠቅሰዋል። “[የኢራን] ጦርነትን ከመቀላቀል ጋር በተያያዘ አቋሜን እንድቀይር ቀላል የማይባል ጫና ደርሶብኛል፤ በጦርነቱ ላይ አቋሜን አልቀይርም” ሲሉ ተናግረዋል።

    “ጫናው ምንም ይሁን ምን፣ ጫጫታው ምንም ቢሆን እኔ የብሪታኒያ ጠቅላይ ሚኒስትር ነኝ፤ በብሔራዊ ጥቅማችን መሠረት መንቀሳቀስ አለብኝ” ብለዋል።

    በዚህ የለንደን አቋም ያልተደሰቱት ፕሬዝዳንት ትራምፕ ማክሰኞ ዕለት በትሩዝ ሶሻል ማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት ጽሁፍ ዩናይትድ ኪንግደምን ጨምሮ ለአጋር አገራት መልዕክት አስተላልፈዋል። “እንዴት ለራሳችሁ መዋጋት እንዳለባችሁ መማር መጀመር አለባችሁ፤ ከአሁን በኋላ አሜሪካ ለማገዝ አትደርስላችሁም” ሲሉ ጽፈዋል።

  7. ትራምፕ አሜሪካን ከኔቶ የማስወጣት ጉዳይን “አጥብቀው እያሰቡበት” መሆኑን ተናገሩ

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ፤ የሰሜን አትላንቲክ የጦር ቃል ኪዳን ድርጅት (ኔቶ) በኢራን ጦርነት እገዛ እንዲያደርግላቸው ያቀረቡትን ጥሪ ባለመቀበሉ አሜሪካን ከወታደራዊው ጥምረት ማስወጣትን አጥብቀው እያሰቡበት እንደሆነ ለብሪታኒያው ጋዜጣ ‘ዘ ቴሌግራፍ’ ተናገሩ።

    ኔቶን “የወረቀት ላይ ነብር” ሲሉ የጠሩት ትራምፕ፤ አሜሪካን ከመከላከያ ስምምነቱ የማስወጣት ሃሳብ “ከማጤን መሻገሩን” መናገራቸውን ዘገባው አመልክቷል።

    የብሪታኒያው ጋዜጣ ከጦርነቱ በኋላ አሜሪካን ከኔቶ አባልነት የማስወጣት ዕቅድ ይዘው እንደሆን ጠይቋቸዋል። ትራምፕ ሲመልሱ፤ “አዎ፤ ከማጤን ባሻገር ጊዜው ደርሷል ብዬ መናገር እችላለሁ። የወረቀት ላይ ነብር እንደሆኑ ሁሌም አውቅ ነበር፤ በነገራችን ላይ ፑቲንም ይህንን ያውቃል” ብለዋል።

    በአሜሪካ እና እስራኤል ጦርነት የተከፈተባት ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥን በመዝጋት የዓለም የኤነርጂ እቅርቦት ቅርቃር ውስጥ እንዲገባ አድርጋለች። በዚህ ምክንያት ጫና የበረታባቸው ፕሬዝዳንት ትራምፕም ኔቶ እና አጋሮቻቸው ወሽመጡን ለማስከፈት እገዛ እንዲያደርጉ ሲጠይቁ ሰንብተዋል። ከኔቶም ሆነ ከአገራት ያገኙት ምላሽ ግን አዎንታዊ አልሆነም።

    ትራምፕ ከጋዜጣው ጋር በነበራቸው ቃለ መጠይቅ ኔቶ ሊያግዛቸው አለመንቀሳቀሱ “ለማመን የሚከብድ” እንደሆነ ተናግረዋል። ጥምረቱን ለማሳመን ያን ያህል አለመጎትጎታቸውን የተናገሩት ትራምፕ፤ ወዲያውኑ መንቀሳቀስ ነበረባቸው ብለው እንደሚያምኑ ገልጸዋል።

    “ዩክሬንን ጨምሮ ወዲያውኑ ነበር የደረስንላቸው። ዩክሬን ችግራችን አልነበረችም። ፈተና ነበር፤ እኛም ደርሰንላቸዋል። ሁሉም ቢሆን ስንደርስላቸው ነበር። ለእኛ [ግን] አልደረሱልንም” ሲሉ ለቴሌግራፍ ተናግረዋል።

    ትራምፕ በዚህ ቃለ መጠይቃቸው በጦርነቱ እንደማትሳተፍ የገለጸችላቸውን ዩናይትድ ኪንግደምንም ወርፈዋል። “የባሕር ኃይል እንኳን የላችሁም። በጣም አርጅታችኋል፤ አውሮፕላን ጫኝ መርከቦቻችሁን አይሠሩም” ብለዋል።

  8. ሁለት ሦስተኛ የሚሆኑት አሜሪካውያን የኢራን ጦርነት በቶሎ እንዲያበቃ እንደሚፈልጉ ጥናት አሳየ

    ከአሜሪካ ዜጎች ሁለት ሦስተኛ የሚሆኑት የትራምፕ አስተዳደር ያስቀመጣቸው ግቦች ሳይሳኩም ቢሆን አገራቸው በኢራን ጦርነት ውስጥ ያላት ተሳትፎ በቶሎ እንዲያበቃ እንደሚፈልጉ የሕዝብ አስተያየት ዳሰሳ ማሳየቱን የዜና ወኪሉ ሮይተርስ ዘገበ።

    ሮይተርስ እና የሕዝብ አስተያየት ኩባንያው ‘አይፒኤስኦኤስ’ ባደረጉት ዳሰሳ ከተሳተፉ አሜሪካውያን ውስጥ 66 በመቶው ጦርነቱ እንዲቆም ፍላጎት እንዳላቸው ገልጸዋል። 27 በመቶ ያህሉ ደግሞ ጦርነቱ ለተራዘመ ጊዜ ቢቆይም እንኳ አሜሪካ ሁሉንም ግቦቿን ለማሳካት መሥራት አለባት የሚል ምላሽ መስጠታቸውን ዘገባው ያመለክታል።

    ዘገባው እንደሚያሳየው፤ የፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ደጋፊ ከሆኑ ሪፐብሊካኖች መካከል 40 በመቶ ያህሉ ግቦች ሳይሳኩም ቢሆን ጦርነቱ በቶሎ እንዲቋጭ ይፈልጋሉ። 57 በመቶው በአንጻሩ አሜሪካ በጦርነቱ ውስጥ ለተራዘመ ጊዜ መቆየቷን ይደግፋሉ።

    አንድ ወር በተሻገረው የኢራን ጦርነት ምክንያት መካከለኛው ምሥራቅ ውስጥ በሺህዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ተገድለዋል። በኤነርጂ ዘርፍ ላይ ክርኑን ያጠነከረው ጦርነት የነዳጅ አቅርቦት እንዲስተጓጎል እና ዋጋውም እንዲንር ምክንያት ሆኗል። በዓለም አቀፍ ደረጃ የዋጋ ግሽበትን ያባብሳል የሚል ስጋትም ተፈጥሯል።

    በጥናቱ ከተሳተፉ 60 በመቶ አስተያየት ሰጪዎች ውስጥ 60 በመቶው ለጦርነቱ ጅማሬ ምክንያት የሆነውን የአሜሪካ ጥቃትን አይቀበሉትም። በዳሰሳው ከተሳተፉት ከአንድ ሺህ በላይ ሰዎች መካከል 35 በመቶው ደግሞ በኢራን ላይ የተፈጸመውን ጥቃት እንደደገፉ ሮይተርስ ዘግቧል።

  9. በኤምሬትስ፣ በኳታር፣ በባህሬን፣ በሳዑዲ አረቢያ እና በኩዌት ላይ የቀጠለው የኢራን ጥቃት

    በእስራኤል እና በአሜሪካ ጥቃት ስር የምትገኘው ኢራን ወደ እስራኤል ከምትተኩሳቸው ሚሳዔሎች በተጨማሪ በባሕረ ሰላጤው አገራት ላይ በአጸፋ የምትወስደው እርምጃ ቀጥሏል።

    ኤምሬትስ: ከኢራን የተተኮሰ ሚሳዔል ተመትቶ ሲከሽፍ ስብርባሪው የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ ውስጥ ነዋሪ የሆነ አንድ ባንግላዲሻዊ ሠራተኛን ገድሏል።

    ኳታር: የዩናይትድ ኪንግደም የባሕር ትራንስፖርት ንግድ ማዕከል እንዳስታወቀው አንድ ነዳጅ ጫኝ መርከብ ከኳታር የባሕር ዳርቻ ወጣ ብሎ በሚገኝ የውሃ አካል ላይ “በሁለት ተወንጫፊዎች” ተመትቷል።

    ባህሬን: የአደጋ ማስጠንቀቂያ ደወል ዛሬ ጠዋት የተሰማ ሲሆን፣ የኳታር የአገር ውስጥ ጉዳይ እና የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች “በኢራን ጥቃት የተነሳን እሳት” ለማጥፋት መሰማራታቸውን አስታውቋል።

    ሳዑዲ አረቢያ: የመከላከያ ሚኒስቴሯ ዛሬ ጠዋት ሁለት ድሮኖችን እና ትናንት ሌሊት ሌሎች ተጨማሪ ድሮኖችን መትቶ ማክሸፉን አስታውቋል።

    ኩዌት: የአገሪቱ ሲቪል አቪዬሽን ባለሥልጣን እንዳለው በዋና ከተማዋ ባለው ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ውስጥ የሚገኝ የነዳጅ ማከማቻዎች በኢራን ድሮኖች ዒላማ መደረጋቸውን አሳውቋል። ጨምሮም በጥቃቱ “ከፍተኛ እሳት” ተነስቶ “ከፍተኛ ጉዳት” ቢደርስም በሰው ላይ የደረሰ ጉዳት እንደሌለ ተገልጿል።

  10. ሊባኖስ ላይ ተጠናክሮ የቀጠለው የእስራኤል ጥቃት

    ከባድ ወታደራዊ ዘመቻ እየተካሄደ ባለባት የሊባኖስ ዋና ከተማ ቤይሩት ውስጥ አንድ የሄዝቦላህ አዛዥ እና ሌላ ከፍተኛ አመራር ጥቃት እንደተፈጸመባቸው የእስራኤል ጦር አስታወቀ።

    ጦሩ ሌሊቱን ቤይሩት ውስጥ በሁለት ቦታዎች ላይ ጥቃት መፈጸሙን የገለጸ ሲሆን በከተማዋ ውስጥ በርካታ ፍንዳታዎች መሰማታቸውን የደኅንነት ባለሥልጣናት ለሮይተርስ ዜና ወኪል ተናግረዋል።

    ከዋና ከተማዋ በስተደቡብ ሲጓዝ የነበረ አንድ መኪና ከእስራኤል ድሮን በተወነጨፉ በርካታ ሚሳዔሎች መመታቱን የአገሪቱ መንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘግቧል።

    በሊባኖስ ደቡባዊ ክፍል ማክሰኞ ዕለት በተፈጸመ ጥቃት የሕክምና ባለሙያዎችን ጨምሮ ቢያንስ ሰባት ሰዎች መገደላቸውን የአገሪቱ ጤና ሚኒስቴር አስታውቋል።

    አንድ ወር ባለፈው እስራኤል ሊባኖስ ውስጥ እያካሄደችው ባለው ወታደራዊ ጥቃት እስካሁን ድረስ ቢያንስ 1,200 ሰዎች ሲገደሉ 1.2 ሚሊዮን የሚሆኑ ሰዎች ደግሞ ተፈናቅለዋል።

  11. ቻይና እና ፓኪስታን የኢራንን ጦርነት ለመቋጨት ባለ አምስት ነጥብ የስምምነት ዕቅድ አቀረቡ

    ቻይና እና ፓኪስታን፤ የኢራንን ጦርነት ለመቋጨት አፋጣኝ ተኩስ አቁም ማድረግን እንዲሁም የሆርሙዝ ወሽመጥ መልሶ መክፈትን የሚያካትት ባለ አምስት ነጥብ የስምምነት ዕቅድ አቀረቡ።

    የሰላም ዕቅዱ የተረቀው የፓኪስታነው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አገራቸው ጦርነቱን እንዲያበቃ ለማደራደር በምታደርገው ጥረት የቻይናን ድጋፍ ለመጠየቅ ወደ ቤይጂንግ ከተጓዙ በኋላ ነው።

    የቻይና ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር እንደገለጸው ሁለቱ አገራት “ሰላምን ለማስፈን አዲስ ጥረት” እያደረጉ ነው።

    ቻይን የኢራን ጦርነትን በተመለከተ እስካሁን ድረስ የሰጠችው ምላሽ የቀዘቀዘ ነው። ከፍተኛ የነዳጅ ክምችት ያላት ቻይና ከሌሎች የእስያ አገራት በተለየ ለከፋ የነዳጅ እጥረት የተጋለጠች አይደለችም።

    ይሁን እንጂ ቀውሱ የሚቀጥል ከሆነ ለዓለም ገበያ ምርት የሚያቀርቡ ፋብሪካዎች የሚገኙበት የቻይና የኢንዱስትሪ እምብርት በረጅም ጊዜ ሂደት ተጽዕኖ ሊደርስበት ይችላል የሚል ስጋት አለ።

    ይልቁንም የኢራን ጦርነት ጥላውን ያጠላው የፕሬዝዳንት ዢ ሺፒንግ መሻት በሆነው መረጋጋት ላይ ነው። ቻይና እንድታድግ እና ምርቶቿን ለውጭ አገራት እንድታቀርብ ከተፈለገ የዓለም ኢኮኖሚ መረጋጋት የሰፈነበት ሊሆን ይገባል።

    አሁን የኢራን ጦርነት ከአንድ ወር በላይ ለሚሆን ጊዜ መሻገሩን ተከትሎ የነዳጅ ዋጋ እያሻቀበ ነው። የቻይና መንግሥትም ተኩስ አቁም ላይ እንዲደረስ የሚያደርገውን ጥረት አሳድጓል።

    የአገሪቱ መንግሥት ከዚህ ቀደምም በመካለኛው ምሥራቅ የሰላም ፈጣሪነት ሚናን ሲጫወት ነበር፤ ይህም በአውሮፓውያኑ 2023 ሳዑዲ አረቢያ እና ኢራን ስምምነት ላይ እንዲደርሱ ያደረገ ሲሆን በዚህም አገራቱ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነታቸውን ጀምረዋል።

    ከአንድ ዓመት በኋላ ደግሞ ከ14 የፍልስጤም ክንፎች የተወጣጡ መሪዎችን ሰብስቦ የብሔራዊ አንድነት መንግሥት እንዲመሠረት አድርጓል።

    የአሁኑን የስምምነት ዕቅድ በተመለከተ እስካሁን ድረስ ይህ ነው የሚባል የተቀባይነት ምልክት አልታየም። ነገር ግን ይህ ተነሳሽነት እንዲቀጥል ግፊት ማድረግ ፕሬዝዳንት ዢ፤ ከሌሎቹ የዓለም ኃያል አገራት መሪዎች ሲነጻጸሩ ገለልተኛ አደራዳሪ እና ሰላም ፈጣሪ ሆነው እንዲወጡ ያስችላቸዋል።

  12. ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥ ሲከፈት ለአሜሪካ፣ ለእስራኤል እና ለአጋሮቻቸው ዝግ እንደሚሆን አሳወቀች

    ሆርሙዝ ወሽመጥ እንደሚከፈት ነገር ግን ለአሜሪካ፣ ለእስራኤል እና ለደጋፊዎቻቸው ዝግ እንደሚሆን የኢራን ፕሬዝዳንት እና የአገሪቱ ፓርላማ የብሔራዊ ደኅንነት ኮሚቴ ሰብሳቢ ተናገሩ።

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከኢራን ጋር የሚደረገው ጦርነት በጥቂት ሳምንታት ውስጥ እንደሚያበቃ እየተናገሩ ባሉበት በአሁኑ ወቅት፤ የኢራን ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዜሽኪያን የሆርሙዝ ወሽመጥ “ለጠላቶች እና ለደጋፊዎቻቸው” ዝግ ሆኖ ይቆያል ብለዋል።

    የኢራን ፓርላማ የብሔራዊ ደኅንነት ኮሚቴ ሰብሳቢ ኢብራሂም አዚዚም በተመሳሳይ የባሕር መተላለፊያው ለሌሎች አገራት እንደሚከፈት ነገር ግን ለአሜሪካ ዝግ እንደሚሆን አሳውቀዋል።

    ፕሬዝዳንት ፔዜሽኪያን ከአውሮፓ ምክር ቤት ፕሬዝዳንት አንቶኒዮ ኮስታ ጋር እየተካሄደ ስላለው ጦርነት በስልክ ውይይት ባደረጉበት ጊዜ ከአሜሪካ እና ከእስራኤል በተጨማሪ በጦርነቱ ድጋፍ ያደረጉ አገራትም በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል እንዲያልፉ እንደማይፈቀድ መናገራቸውን የአገሪቱ መንግሥት ዜና አገልግሎት ኢርና ዘግቧል።

    ፕሬዝዳንት ፔዜሽኪያን በውይይታቸው ወቅት ከፋርስ ባሕረ ሰላጤ አካባቢ ከፍተኛ መጠን ያለው ነዳጅ እና ጋዝ የሚተላለፍበት የሆርሙዝ ወሽመጥ ወራሪዎች ላሏቸው አሜሪካ እና እስራኤል እንዲሁም ደጋፊዎቻቸው ዝግ ሆኖ እንደሚቀጥል በአጽንኦት ተናግረዋል።

    የኢራን ፓርላማ ባለሥልጣን የሆኑት ኢብራሂም አዚዚ ደግሞ በኤክስ ገጻቸው ለፕሬዝዳንት ትራምፕ ባስተላለፉት መልዕክት “የሆርሙዝ ወሽመጥ በእርግጠኝነት ይከፈታል፤ ለእናንተ ግን ዝግ ይሆናል፤ አዲሱን የኢራን ሕግ ለሚያከብሩ ክፍት ይደረጋል” ብለዋል።

    ባለሥልጣኑ ጨምረውም “በመጨረሻም ትራምፕ ‘ሥርዓት ለውጥ እንዲመጣ አድርገዋል’፤ ነገር ግን ይህ ለውጥ በቀጣናው የባሕር መስመር አጠቃቀም ሥርዓት ላይ የመጣ ነው” በማለት ኢራን አዲስ ያወጣችውን ሆርሙዝ መተላለፊያ ሕግን ጠቅሰዋል።

    የኢራን ፓርላማ የብሔራዊ ደኅንነት ኮሚቴ ሰኞ ዕለት ሆርሙዝን ሙሉ ለመሉ በአራን መንግሥት ቁጥጥር ስር የሚያስገባ እና በወሽመጡ በኩል የሚተላለፉ መርከቦች ለኢራን ክፍያ እንዲፈጽሙ የሚያደርግ ሕግ ማውጣቱን ፋርስ የዜና ወኪል ዘግቧል።

    ባለፈው ሳምንት ፕሬዝዳንት ትራምፕ ከኢራን ጋር ለሚደረግ ድርድር ባቀረቡት ባለ 15 ነጥብ ዕቅድ ውስጥ ሆርሙዝ የባሕር ወሽመጥ ዓለም አቀፍ ነጻ የእንቅስቃሴ ቀጣና እንዲሆን የሚጠይቅ ሃሳብ አስገብተው ነበር።

    አሜሪካ እና ወዳጆቿ የሆኑ የመካከለኛው ምሥራቅ አገራት ኢራን በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ የሚኖራትን ተጽእኖ በከፍተኛ ሁኔታ እንዲገደብ ፍላጎት ያላቸው ቢሆንም ኢራን ግን መተላለፊያው ላይ ያላትን ቁጥጥር እያጠበቀች ነው።

  13. የኢራን ፕሬዝዳንት ጦርነቱን ለማቆም ጥቃት እንደማይደገም መተማመኛ መቅረብ አለበት አሉ

    የኢራን ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዜሽኪያን የተወሰኑ ቅድመ ሁኔታዎች እስከተሟሉ ድረስ አገራቸው ከአሜሪካ እና ከእስራኤል ጋር የሚደረገውን ጦርነት ለማቆም “አስፈላጊው ፈቃደኝነት” እንዳላት ተናገሩ።

    ፕሬዝዳንቱ የአሜሪካ ገበያ ዋጋ እንዲጨምር ያደረገውን ይህንን አስተያየታቸውን የሰጡት ከአውሮፓ ምክር ቤት ፕሬዝዳንት ጋር ባደረጉትን የስልክ ንግግር ነው።

    ፔዜሽኪያን “ወሳኝ ሁኔታዎች፤ በተለይ ጥቃት እንዳይደገም ለመከላከል የሚያስችል መተማመኛ እስከተሟላ ድረሰ፤ ይህንን ግጭት ለማቆም አስፈላጊው ፈቃደኝነት አለን” ሲሉ ተናግረዋል።

    “በዚህ ግጭት ውስጥ በማንኛውም ምክንያት የሚደረግ የውጭ ጣልቃ ገብነት ለቀጣናው አደገኛ መዘዝ እንደሚኖረው” ማስጠንቀቃቸውን ጽሕፈት ቤታቸው ያወጣው መግለጫ ያሳያል።

    ፕሬዝዳንቱ አክለውም፤ የአውሮፓ አገራትም ኢራንን በተመለከተ የያዙን ”አውዳሚ አካሄድ በዓለም አቀፍ ሕግ እንዲሁም ገንቢ እና ሙያዊ ግንኙነት ላይ በተመሠረቱ ፖሊሲዎች መተካት እንዳለባቸው” አስገንዝበዋል።

    ኢራን የጎረቤት አገራትን ሉዓላዊነት እንደምታከበር እና እነርሱን የማጥቃት ዓላማ እንደሌላትም ተናግረዋል ተብሏል። “ከእነዚህ አገራት በተወሰኑት ውስጥ የሚገኙ የአሜሪካ የጦር ሠፈሮች ኢራንን ለማጥቃት ጥቅም ላይ እየዋሉ ነው፤ እነዚያ መንግሥታትም እንዲህ ዓይነቱን እርምጃ የመከላከል ኃላፊነታቸውን አላሟሉም” ብለዋል።

    ፔዜሽኪያን አክለውም “አሜሪካ ከልቧ በዲፕሎማሲ አታምንም። የኢራን ሕጋዊ ራስን የመከላከል እርምጃ ተፈጥሯዊ መብት ነው” ማለታቸውን መግለጫው ያስረዳል።

    የአውሮፓ ኅብረት ምክር ቤት ፕሬዝዳንቱ አንቶኒዮ ኮስታ በበኩላቸው ከስልክ ንግግሩ በኋላ በኤክስ ገጻቸው ባወጡት መግለጫ፤ በመካከለኛው ምሥራቅ ያለው ሁኔታ “እጅግ አደገኛ” እንደሆነ ገልጸዋል። ከኢራኑ ፕሬዝዳንት ጋር በነበራቸው ንግግር ውጥረቱን ማርገብ እና ከወታደራዊ እርምጃ መቆጠብ እንደሚገባ ማሳሰባቸውን ተናግረዋል።

    “የሲቪል መሠረተ ልማቶች እንዲጠበቁ” እንዲሁም “ሁሉም ወገኖች ዓለም አቀፍ ሕግን መጠበቅ እንደሚገባቸው” እንዳሳሰቡም ጽፈዋል።

    “ሁኔታውን ለማርገብ፤ ኢራን በቀጣናው አገራት ላይ የምትፈጽማቸውን ተቀባይነት ሌላቸው ጥቃቶች እንድታቆም እና በዲፕሎማሲው መስመር አዎንታዊ ግንኙነት እንዲኖራት አሳስቤያለሁ” ብለዋል።

    በተለይም በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል የሚደረግ ጉዞ ነጻነትን ለማረጋገት ከተባበሩት መንግሥታት ጋር ግንኙነት እንድታደርግ ጠይቀዋል።

  14. እስራኤል ተቆጣጥራ በምትቆየው የሊባኖስ ግዛት ውስጥ የሚገኙ ቤቶችን በሙሉ እንደምታፈርስ ገለጸች

    የእስራኤል መከላከያ ሚኒስትር ኢዝራኤል ካትዝ ሄዝቦላ ላይ የሚካሄደው ጦርነት ከተቋጨም በኋላ አገራቸው ደቡባዊ ሊባኖስ ውስጥ የሚገኝ 30 ኪሎ ሜትር የሚደርስ መሬት ተቆጣጥራ እንደምትቆይ ተናገሩ። ከእስራኤል ጋር በሚጎራበቱ የሊባኖስ መንደሮች የሚገኙ ቤቶች በሙሉ እንደሚፈርሱም የመከላከያ ሚኒስትሩ ገልጸዋል።

    እንደ ኢዝራኤል ካትዝ ገለጻ፤ እስራኤል ወርራ በምትይዘው መሬት የደቡባዊ ሊባኖስ መሬት ውስጥ የደኅንነት ቀጣና የማቋቋም እቅድ አላት።

    መከላከያ ሚኒስትሩ፤ “የዘመቻው ማብቂያ ላይ የእስራኤል መከላከያ ሠራዊት ሊባኖስ ውስጥ የደኅንነት ዞን ያቋቁማል፤ የጸረ-ታንክ ሚሳኤሎችን ለመከላከል በሚያስችል የመከላከያ መስመር ይሰፍራል። የሊታኒ [ወንዝ] አካባቢ በሙሉ ያለውን ደኅንነት ይቆጣጠራል” ብለዋል

    "በተጨማሪም፣ ሰሜናዊ [እስራኤል] ነዋሪዎች ደህንነት እና ዋስትና እስከሚረጋገጥ ድረስ ከሰሜኑ የድንበር አካባቢ ተፈናቅለው የነበሩ ከ600,000 በላይ የደቡብ ሊባኖስ ነዋሪዎች ከሊታኒ በስተደቡብ ወደሚገኘው መኖሪያቸው መመለሳቸው ሙሉ በሙሉ የተከለከለ ነው" ሲሉም ተናግረዋል።

    “በሊባኖስ ድንበር አቅራቢያ በሚገኝ መንደሮች ውስጥ ያሉ ቤቶች በሙሉ በድንበር አቅራቢያ ለሚገኙ የሰሜናዊ እስራኤል ነዋሪዎች ላይ የሚጋርጡትን ስጋት ለአንዴ እና ለመጨረሻ ጊዜ ለማስወገድ ሲባል በጋዛ በነበረው የራፋህ እና ቤይት ሃኑን ሞዴል መሰረት ይፈርሳሉ” ሲሉ የአገራቸውን እቅድ አሳውቀዋል።

    የሊባኖስ መከላከያ ሚኒስትር ሜጀር ጄነራል ሚካኤል ሜናሳ በእስራኤሉ አቻቸው የቀበውን እቅድ ተቃውመዋል። የእስራኤል እቅድ “በሊባኖስ ግዛት ውስጥ አዲስ ወረራን ለመጫን የተያዘውን ግልጽ እቅድ” እንደሚያንጸባርቅም ገልጸዋል።

    እስራኤል ይፋ ያደረገችው እቅድ “ከአሁን ወዲህ ስጋት ብቻ እንዳልሆነ” የተናገሩት የሊባኖስ መከላከያ ሚኒስትር፤ “በመቶ ሺህዎች የሚቆጠሩ ዜጎች በድጋፍ ለማፈናቀል እና በደቡባዊ የአገሪቱ ክፍል የሚገኙ መንደሮች እና ከተሞችን ስልታዊ በሆነ መንገድ ለማጥፋት” የተያዘ እቅድ እንደሆነ ገልጸዋል።

    የተባበሩት መንግሥታት፣ አውሮፓውያን አገራት እና ካናዳም የእስራኤል እቅድ ተችተዋል። ማክሰኞ ዕለት በተካሄደው የተባበሩት መንግሥታት የጸጥታው ምክር ቤት ስብሰባ ላይ ንግግር ያደረጉት በተመድ ረዳት ኃላፊ ቶም ፍሌቸር አሁን የሚታየው የወታደራዊ እርምጃ መባባስ ቀድሞውኑ አስጊ የሆነውን ሁኔታ ይበልጥ አሳሳቢ እንደሚያደርገው ተናግረዋል።

  15. ትራምፕ ከኢራን ጋር ስምምነት ባይደረስም ጦርነቱ በሁለት ወይም በሦስት ሳምንት ውስጥ እንደሚያበቃ ተናገሩ

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አሜሪካ በኢራን ላይ የከፈተችው ጦርነት ከሁለት እስከ ሦስት ሳምንት በሚሆን ጊዜ ውስጥ ይጠናቀቃል አሉ። ኢራን ስምምነት ላይ መድረሷ ጦርነቱን ለማቆም ቅድመ ሁኔታ አለመሆኑንም ገልጸዋል።

    ትናንት በዋይት ሃውስ ከጋዜጠኞች ጋር ቆይታ ያደረጉት ትራምፕ፤ አሜሪካ “እጅግ በቅርቡ” ከኢራን ጋር የገባችበትን ጦርነት እንደምታቆም ጠቁመዋል። አሜሪካ የምትወስደው ወታደራዊ እርምጃ “በሁለት ወይም ሦስት ሳምንት” ጊዜ ውስጥ እንደሚጠናቀቅ ሲናገሩ ተደምጠዋል።

    እንደ ፕሬዝዳንቱ ገለጻ፤ አሜሪካ ከአንድ ወር በፊት ከእስራኤል ጋር በመሆን ጥቃት ከመክፈቷ በፊት ያስቀመጠቻቸውን ግቦች አሳክታለች። ዋነኛው ግብ የኢራንን የኒውክሌር መሣሪያ የመታጠቅ አቅም መገደብ እንደነበር የተናገሩት ትራምፕ፤ አሜሪካ አሁን “ስራውን እያጠናቀቀች” መሆኑን አንስተዋል።

    አሜሪካ የአራንን ሰማይ እንደተቆጣጠረችው እንዲሁም በበርካታ ከፍተኛ ፖለቲካዊ እና ወታደራዊ አመራሮች ግድያ ምክንያት የአገዛዝ ለውጥ መሳካቱንም ተናግረዋል። አዲሶቹን የኢራን አመራሮች ከቀድሞዎቹ አንጻር “አክራሪነታቸው እጅጉን የቀነሰ” እንዲሁም “ይበልጥ ምክንያታዊ” ሲሉ ገልጸዋል።

    የኢራን መሪዎች አሜሪካ ጦርነቱን እንድታበቃ የሚያደርጋት “ስምምነት ላይ ለመድረስ እየለመኑ” ነው ሲሉም ከዚህ ቀደም ኢራን ያስተባበለችውን ንግግራቸውን ደግመዋል።

    እንደ ትራምፕ ገለጻ ከኢራን ጋር ስምምነት ባይደረስም ጦርነቱ ሊቋጭ ይችላል። “ኢራን ስምምነት ላይ መድረስ አይጠበቅባትም። ከእኔ ጋር ስምምነት መፈጸም አይጠበቅባቸውም” ሲሉ ተናግረዋል።

    በፓኪስታን በኩል ባለ 15 ነጥብ የስምምነት እቅድ ወደ ኢራን የላኩት ፕሬዝዳንት ትራምፕ፤ ቴህራን እነዚህ ነጥቦች የማትቀበል ከሆነ ወታደራዊ እርምጃቸውን እንደሚጨምሩ ሲዝቱ ቆይተዋል።

    በስምምነት እቅዱ ላይ ከተቀመጡ ዋነኛ ነጥቦች መካከል፤ ኢራን የኒውክሌር መሣሪያ እንደማይኖራት ቃል እንድትገባ ማድርግ እና ሁሉንም የዩራኒየም ማበልጸግ ተግባሯን እንድታቋርጥ ማድረግ የሚሉት ይገኙበታል።

    የሆርሙዝ ወሽመጥ ሙሉ በሙሉ መከፈቱም ከስምምነት እቅድ ነጥቦች መካከል ነው። ከዓለም የነዳጅ ምርት 20 በመቶ ያህሉ የሚተላለፍበት ይህ ወሳን የባሕር ጉዞ መስመር በመዘጋቱ እና በጦርነቱ ምክንያት በኢነርጂ መሠረተ ልማቶች ላይ በደረሰው ጉዳት የተነሳ በዓለም አቀፍ ደረጃ የነዳጅ ዋጋ ከፍተኛ ጭማሪ አሳይቷል።

    ትራምፕ በትናንቱ ንግግራቸው አሜሪካ ወታደራዊ እርምጃ መውሰድ እንዳቆመች ጦርነቱ በነዳጅ ዋጋ ላያ የፈጠረው ተጽዕኖ እንደሚረግብ ገልጸዋል።

  16. የአውሮፓ አገራት ለአሜሪካ ወታደራዊ አውሮፕላኖች የአየር ክልላቸውን እየዘጉ ነው

    የአውሮፓ አገራት አሜሪካ በኢራን ላይ ለምታካሂደው ወታደራዊ ጥቃት የጦር አውሮፕላኖቿ የአየር ክልላቸውን እንዳይጠቀሙ እየከለከሉ ነው።

    እንዲህ ያለው ውሳኔ በስፔን የተጀመረ ሲሆን፣ አሁን ደግሞ ፈረንሳይ እና ጣልያን ተመሳሳይ አቋም መያዛቸው እየተዘገበ ነው።

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ እንዳሰፈሩት የጦር መሳሪያ ጭነው ወደ እስራኤል የሚበሩ ወታደራዊ አውሮፕላኖቻቸው በአየር ክልሏ በኩል እንዳያልፉ ፈረንሳይ መከልከሏን ጠቅሰው ቅሬታቸውን አሰምተዋል።

    ከአንድ ወር በላይ በኢራን ላይ ያልተቋረጠ ጥቃት እየፈጸሙ ያሉት ፕሬዝዳንት ትራምፕ በፈረንሳይ ውሳኔ ከፉኛ የተቆጡ ሲሆን፣ በጽሁፋቸውም ጠንከር ባለ ሁኔታ የፈረንሳይን ክልከላ “አሜሪካ አትረሳውም” ብለዋል።

    በተጨማሪም ጣልያን ወደ መካከለኛው ምሥራቅ የሚያቀና አንድ የአሜሪካ ወታደራዊ አውሮፕላን ሲሲሊ ውስጥ በሚገኝ ሲጎኔላ የአየር ኃይል ሰፈር እንዳያርፍ መከልከሏን የአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    የጦር ሰፈሩ የጣልያን የአየር ኃይል ሰፈር ሲሆን፣ የአሜሪካ ባሕር ኃይልም የሰፈረበት ነው።

    ቀደም ሲል የስፔን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በኢራን ጦርነት ውስጥ ለሚሳተፉ የአሜሪካ አውሮፕላኖች የአገሪቱ የአየር ክልል ዝግ መደረጉን አሳውቋል።

  17. በዓለም ዙሪያ የነዳጅ ዋጋን ያናረው የኢራን ጦርነት

    አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ ጦርነት ከከፈቱ አንስቶ የዓለም አቀፍ የነዳጅ ዋጋ መነሻ በሆነው የብሬንት የግብይት መድረክ ላይ ድፍድፍ ነዳጅ በበርሜል ከ73 ዶላር ተነስቶ ወደ 117 ዶላር አሻቅቧል።

    ይህ በጅምላ የነዳጅ አቅርቦት ላይ የታየው የዋጋ ጭማሪ በዓለም ዙሪያ በሚገኙ የነዳጅ ተጠቃሚዎች ላይም ተንጸባርቋል።

    ጦርነቱ ከተቀሰቀሰበት ጊዜ ጀምሮ በአሜሪካ የነዳጅ ዋጋ በአማካይ ከአንድ ዶላር በላይ ጭማሪ ሲያሳይ፣ በጋሎን ወደ አራት ዶላር በመድረስ በአራት ዓመታት ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ ከፍተኛው ነው ተብሏል።

    ዩናይትድ ኪንግደም ውስጥ አማካይ የቤንዚን ዋጋ በ14 በመቶ ጭማሪ ሲያሳይ፣ የናፍጣ ዋጋ ደግሞ በ27 በመቶ ጨምሯል።

    በባሕረ ሰላጤው ጦርነት ምክንያት ተፈጠረው የነዳጅ አቅርቦት መስተጓጎል በሌሎች አገራት ውስጥም የነዳጅ እጥረት እና የዋጋ ጭማሪን በማስከተሉ አገራት አማራጭ እርምጃዎችን እየወሰዱ ነው።

    ሲሪ ላንካ እና ባንግላዴሽን የመሳሰሉ አገራት ነዳጅ በሬሽን መልክ ማከፋፈል የጀመሩ ሲሆን፣ ስሎቫኪያ ደግሞ ባለፈው ሳምንት ተመሳሳይ እርምጃ በመውሰድ የመጀመሪያዋ የአውሮፓ አገር ሆናለች።

    በአውስትራሊያ ውስጥ ደግሞ የአሽከርካሪዎችን የነዳጅ ዋጋ ጫና ለማቅለል በነዳጅ ላይ የተጣለው የኤክሳይዝ ታክስ ለሦስት ወራት በግማሽ እንዲቀንስ ተደርጓል።

    እንዲሁም ሁለት የአውስትራሊያ ግዛቶች ዜጎች የግል መኪኖቻቸውን እንዳያሽከረክሩ ለማበረታታት ለጊዜው የሕዝብ ትራንስፖርት በነጻ እንዲሆን አድርገዋል።

  18. ኢራን የእስራኤል እና የአሜሪካ ወታደራዊ ማዕከላትን መምታቷን ገለጸች

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ አዲስ በከፈተው ጥቃት በቀጣናው የሚገኙ የእስራኤል እና የአሜሪካ ወታደራዊ ሰፈሮችን መምታቱን አስታወቀ።

    88 የድሮን እና የሚሳዔል ጥቃት በተፈጸመበት አዲስ ዙር ጥቃት የተለያዩ የእስራኤል እና የአሜሪካ ወታደራዊ ሰፈሮች ዒላማ መደረጋቸውን ገልጿል።

    “የአየር ኃይላችን በኢማድ፣ በኮራምሽሀር 4 እና በቃዳር በተለያዩ ሚሳዔሎች ጥቃት ፈጽሟል” ሲል የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ባወጣው መግለጫ አትቷል።

    በእስራኤል ውስጥ “ማዕከላዊ፣ ሰሜናዊ እና ደቡባዊ” ክፍል የሚገኙ ዒላማዎች መምታቱንም አክሏል። ይህም “የወታደራዊ አዛዦች ዋነኛ የግንኙነት ማዕከልን” እንደሚያካትት ተገልጿል።

    በእስራኤል ጥቃት ተፈጽሟል የተባለባቸው ቦታዎች ቤኒ ብሬክ፣ ቴል አቪቭ፣ ቤርሼባ፣ ጋሊሊ፣ ኔጌቭ፣ ቴል ኖፍ የአየር ኃይል ሰፈር፣ አራድ እና የሙት ባሕር ደቡባዊ ክፍል ናቸው።

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ባወጣው መግለጫ “ተከታታይ በሆነው ስኬታማ ኦፕሬሽን የአሜሪካ ኃይሎች መሸሸጊያዎች፣ በአል-ዳህፋ [አቡ ዳቢ]፣ ቪክቶሪያ [ባግዳድ] እና አሊ ሳሊም [ኩዌት] የሚገኙ የሰው አልባ አውሮፕላን መቆጣጠሪያ ማዕከላት በድሮኖች እና ዒላማ በሚለዩ ሚሳዔሎች ተመትተዋል” ብሏል።

    በእስራኤል ሰሜናዊ እና ደቡባዊ ክፍል እንዲሁም በሰሜናዊ እና ማዕከላዊ ኢራቅ በሚገኙ የአሜሪካ አዛዦች መሸሸጊያዎች እና ዋና መቀመጫዎች “የሊባኖሱ ሄዝቦላህ እንዲሁም በኢራቅ እና የመን የሚገኙ ኢስላሚክ ሬዚስታንስ ኃይሎች ከ120 በላይ ስኬታማ ኦፕሬሽን አካሂደዋል” ሲልም አክሏል።

  19. “በሆርሙዝ ወሽመጥ ከዚህ ቀደሙ በበለጠ መርከቦች እያለፉ ነው”- የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር

    የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ፒት ሄግሴት፤ በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ከዚህ ቀደም ከነበረው “በበለጠ” መርከቦች እየተላለፉ መሆኑን ተናገሩ።

    ዛሬ ለጋዜጠኞች መግለጫ የሰጡት መከላከያ ሚኒስትሩ፤ ስለ ኢራን እና አሜሪካ ድርድር ተጠይቀው “ድርድሩ እውነተኛ ነው፤ እየተካሄደ ነው፤ እየጎለበተ ነው” ሲሉ ተናግረዋል።

    በኢራን “የሥርዓት ለውጥ ተደርጓል” ያሉት ፒት ሄግሴት “የአሁኑ አስተዳደር ከቀደመው በበለጠ ብልህ ነው” ብለዋል።

    ከፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ጋር ስምምነት ላይ ካልተደረሰ ግን በኢራን ላይ የሚፈጸመው ጥቃት “ተባብሶ እንደሚቀጥል” አስጠንቅቀዋል።

    በመግለጫው ላይ ማብራሪያ የሰጡት የአሜሪካ ጥምር ኃይል ዋና ኃላፊ ዳን ኬን፤ 150 የኢራን መርከቦችን መውደማቸውን እና በ30 ቀናት ውስጥ ከ11,000 በላይ ዒላማዎች መመታታቸውን ገልጸዋል።

    የመከላከያ ሚኒስትሩ በበኩላቸው በቅርቡ የአሜሪካ ወታደሮችን እንደጎበኙ ጠቅሰው “ሥራቸውን ለማጠናቀቅ ጉጉት አላቸው” በማለት ገልጸዋቸዋል።

    በአፍጋኒስታን እና በኢራቅ ከታየው የወታደሮች ስምሪት በተለየ ሁኔታ ወታደሮቹ “የተነቃቁ እና ተልዕኳቸው ላይ ያተኮሩ ናቸው” ሲሉም አክለዋል።

  20. ትራምፕ የአውሮፓ አገራት ወደ ሆርሙዝ ወሽመጥ ሄደው ‘ነዳጃቸውን እንዲወስዱ’ አሳሰቡ

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ፤ ዩናይትድ ኪንግደም፣ ፈረንሳይ እና ሌሎችም አገራት ወደ ሆርሙዝ ወሽመጥ በመሄድ ‘ነዳጃቸውን እንዲወስዱ’ መልዕክት አስተላለፉ።

    “ሄዳችሁ የራሳችሁን ነዳጅ ውሰዱ፤ በቃ ውሰዱት” ሲሉ ትራምፕ በትሩዝ ሶሻል የማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ጽፈዋል።

    ፈረንሳይ “የጦር መሣሪያ ጭነው ወደ እስራኤል የሚጓዙ አውሮፕላኖች በአየር ክልሏ እንዳያልፉ አግዳለች” ሲሉም አገሪቱን ወቅሰዋል።

    “ፈረንሳይ እያገዘችን አይደለም። ግን ‘የኢራን ጠላት’ ተወግደዋል” ሲሉም ትራምፕ ተናግረዋል።

    ትራምፕ በማኅበራዊ ሚዲያቸው ፈረንሳይን በጽኑ አውግዘው “አሜሪካ ይሄንን አትዘነጋም” ብለው ዝተዋል።

    ዩናይትድ ኪንግደምን ጨምሮ ሌሎችም በሆርሙዝ ወሽመጥ መዘጋት የነዳጅ አቅርቦት መስተጓጎል የገጠማቸው አገራት ወደ ወሽመጡ ሄደው ‘ነዳጃቸውን እንዲወስዱ’ ፕሬዝዳንቱ አሳስበዋል።

    “ለራሳችሁ መታገልን መማር መጀመር አለባችሁ። ከዚህ በኋላ አሜሪካ አትረዳችሁም። እንዳልደረሳችሁልን ሁሉ እኛም አናግዛችሁም” ብለዋል።

    ትራምፕ የኢራንን አስተዳደር “መበጣጠስ” እንደተቻለ ገልጸው “ከባዱን ደረጃ አልፈናል። ሂዱ እና ነዳጃችሁን ውሰዱ” በማለት ለአገራቱ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።