ዩናይትድ ኪንግደም የሆርሙዝ ወሽመጥን ለማስከፈት ያለመ ጉባዔን ልታስተናግድ ነው

የፎቶው ባለመብት, Reuters
ዩናይትድ ኪንግደም 30 አገራት የሚሳተፉበት እና የሆርሙዝ ወሽመጥን ዳግም ለማስከፈት ያለመ ጉባዔን ልታስተናግድ ነው።
ጉባዔው የዓለም 20 በመቶ ነዳጅ የሚተላለፍበትን ይህንን የባሕር መስመር ለማስከፈት የሚኖሩ ዲፕሎማሲያዊ እና ፖለቲካዊ አማራጮች ላይ ይነጋገራል ተብሎ እጠበቃል።
ኢራን፤ አሜሪካ እና እስራኤል በጋራ ጦርነት ከከፈቱባት ወዲህ በወሽመጡ ላይ የሚንቀሳቀሱ በርካታ መርከቦች ላይ ጥቃት ሰንዝራለች።
በወሽመጡ ላይ የሚደረገው የመርከብ እንቅስቃሴ በዚህ የተነሳ ክፉኛ መስተጓጎሉ ተገልጿል።
ረቡዕ ዕለት የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ መተላለፊያውን ዳግም ለማስከፈት “ቢዘገዩም ወኔያቸውን ማጠናከር አለባቸው" ብለዋል።
ትራምፕ አጋሮቻቸውን ሆርሙዝን ማስከፈት “አስቀድመው ሊያደርጉት ይገባ ነበር” ያሉ ሲሆን፣ አክለውም “ወደ ወሽመጡ ሄዱ፤ እና ውሰዱ፤ ተከላከሉ። ለራሳችሁ ተጠቀሙበት” ብለዋል።
ዋሽንግተን በተደጋጋሚ አጋሮቿን ወሽመጡን ለመከላከል ወይም ጦርነቱ ለመደገፍ የሚጠበቅባቸውን ያህል አልተወጡም በማለት ስትኮንን ቆይታለች።
ዩናይትድ ኪንግደም እና ሌሎች አገራት ይህንን የዋሽንግተን ትችት ተከትሎ ወሽመጡን ለመጠበቅ በጦርነቱ ውስጥ ሳይሳተፉ ምን ማድረግ እንዳለባቸው እንዲመለከቱ አስገድዷቸዋል።
የዩናይትድ ኪንግደም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የቬት ኩፐር ሐሙስ ዕለት በበይነ መረብ የሚካሄደውን ጉባዔ ይመራሉ ተብሏል።
ጉባዔው መጋቢት ወር አጋማሽ ላይ ኢራን በንግድ መርከቦች ላይ የምትፈጽመውን ጥቃት እንድታቆም የፈረሙ አገራትን ያካትታል ተብሎ ይጠበቃል።
የአገራቱ መግለጫ በተወሰኑ የባሕረ ሰላጤው አገራት እንዲሁም በፈረንሳይ፣ ጀርመን፣ ጃፓን፣ አውስትራሊያ እና ሌሎች ድጋፍ አግኝቶ ነበር።
ይህ በእንዲህ አንዳለ የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ጥቃት ከከፈቱባቸው አገራት ወይም ከእነርሱ ጋር ግንኙነት ካላቸው ውጪ ወሽመጡ ለሌሎች መርከቦች ክፍት መሆኑን ተናግረዋል።
ኒውዝሩም አፍሪካ ከተባለ የቴሌቪዥን ጣቢያ ጋር ቃለ ምልልስ ያደረጉት ቃል አቀባዩ እስማኤል ባግሃዒ፣ "ከባለሥልጣኖቻችን ጋር አስፈላጊው ትብብር ከተደረገ በኋላ" መርከቦች እንዲያልፉ ይደረጋሉ ብለዋል።


















