ቀጥታ, አሜሪካ ኢራን ውስጥ ተዋጊ ጄት ሲያበርር የተመታውን አብራሪዋን ታደገች

አርብ ዕለት በደቡባዊ ኢራን ተመትቶ የወደቀውን የአሜሪካ ተዋጊ ጄት ሲያበርሩ ከነበሩ ሁለት ሰዎች ውስጥ ሲፈለግ የነበረው የአየር ኃይል አባል መገኘቱን ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አስታወቁ። ጠፍቶ የነበረውን የአየር ኃይል አባል “እጅግ የተከበረ ኮሎኔል” ሲሉ የገለጹት ትራምፕ፤ “በኢራን አደገኛ ተራሮች ውስጥ ከጠላት መስመር ጀርባ ሆኖ፣ በጠላቶቻችን እየታደነ” ነበር ብለዋል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ኦማን በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል መርከቦች እንዲያልፉ ከኢራን ጋር እየተነጋገረች መሆኗን ገለጸች

    የሆርሙዝ ወሽመጥ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ኢራን፤ ቁልፍ የዓለም አቀፍ የመርከብ ጉዞ መስመር የሆነውን የሆርሙዝ ወሽመጥ መዝጋቷ የኤነርጂ ዋጋ እንዲንር እንዲሁም በዓለም ኢኮኖሚ ላይ እየጨመረ ያለ ጫና እንዲያርፍ አድርጓል።

    ወሽመጡን ከኢራን ጋር የምትጎራበተው ኦማን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በኤክስ ገጹ ባጋራው ልጥፍ፤ ከቴህራን ባለሥልጣናት ጋር ንግግር እየተደረገ መሆኑን ገልጿል። እንደ መስሪያ ቤቱ ገለጻ የኢራን ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እና ኦማን ተገናኝተው በወሽመጡ በኩል “የተሳለጠ” የመርከቦች ጉዞ “ሊረጋገጥ የሚችልባቸው አማራጮችን” በተመለከተ ተወያይተዋል።

    ዛሬ እሁድ የተደረገው ንግግር ከሁለቱም ወገኖች የተወጣጡ ባለሙያዎችን ያካተተ እንደሆነ የገለጸው የኦማን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መተላለፊያውን በተመለከተ “በርካታ ርዕዮች እና እቅዶች” እንደቀረቡም አስታውቋል።

    ሁለቱ አገራት የሆርሙዝ ወሽመጥ በተመለከተ የመከሩት የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ወሳኙ የመርከብ መተላለፊያ ሰኞ ዕለት የማይከፈት ከሆነ ኢራን ላይ “ሲኦልን” እንደሚያዘንቡ በዛቱ ማግሥት ነው።

  2. ትራምፕ፤ ኢራን የተዋጊ ጄት አብራሪውን ለማግኘት “እየተቃረበች ነበር” አሉ

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ፤ የኢራን ጦር በግዛቱ ውስጥ ተመትቶ የወደቀውን የአሜሪካ ተዋጊ ጄት አባል ለማግኘት “ከፍተኛ ቁጥር” ያለው ኃይል አሰማርቶ እና ወታደሩን ለማግኘት “እየተቃረበ” እንደነበር ገለጹ።

    አሜሪካ ከአርብ ዕለት ጀምሮ ስትፈልገው የነበረውን የአየር ኃይል አባሏን ማግኘቷን ዛሬ ጠዋት አስታውቃለች። ትራምፕ በትሩዝ ሶሻል ገጻቸው ባሰፈሩት አዲስ መልዕክት “በከፍተኛ ሁኔታ የተጎዳውን እና እጅግ ጀግና የሆነውን የኤፍ-15 አባል/መኮንን ከኢራን ተራራሮች ጥልቅ ውስጥ ታድገነዋል” ብለዋል።

    ፕሬዝዳንቱ “እጅግ የተከበረ ኮሎኔል” ሲሉ የገለጹትን ወታደር፤ የኢራን ጦር “አጥብቆ፣ በብዙ ቁጥር እየፈለገው እና [ለማግኘትም] እየተቃረ ነበር” ሲሉ ጽፈዋል።

    አሜሪካ ወታደሯን ለማግኘት በርካታ አውሮፕላኖችን እና በመቶዎች የሚቆጠሩ ወታደሮቿን አሰማርታ ነበር። ዘመቻው የሚካሄደው በኢራን ግዛት ውስጥ በመሆኑም አደገኛ እንደሚሆን ባለሙያዎች ሲገልጹ ነበር።

    ትራምፕም በልጥፋቸው “ይህ አይነቱ ስምሪት ‘በሰው እና መሣሪያ’ ላይ በሚያመጣው አደጋ ምክንያን ብዙውን ጊዜ የማይሞከር” እንደሆነ ገልጸዋል።

    “ሁለተኛው ስምሪት የተደረገው አብራሪውን በእኩለ ቀን ከታደግንበት ከመጀመሪያው [ዘመቻ] በኋላ ነው፤ [የመጀመሪያው ስምሪት] ያልተለመደ እና በኢራን ሰማይ ላይ ሰባት ሰዓታትን ያሳለፍንበት ነው” ብለዋል።

    ዘመቻውን “አስገራሚ የጀግንነት እና ተሰጥኦ ትዕይት” ሲሉ ገለጹት ትራምፕ፤ ነገ ሰኞ ጋዜጣዊ መግለጫ እንደሚሰጡ አስታውቀዋል።

  3. የኢራን ኢንተርኔት መቋረጥ በዓለም ረጅሙ ሆኖ ተመዘገበ

    የኢራንን ኢንተርኔት መቋረጥ የሚያሳይ ግራፍ

    የፎቶው ባለመብት, NetBlocks

    የኢራን ግንኙነት መቋረጥ አቀፍ ደረጃ የተደረገ ረጅሙ የኢንተርኔት መዘጋት ሆኖ መመዝገቡን የኢንተርኔት ክትትል ቡድኑ ኔትብሎክስ አስታወቀ።

    የኔትብሎክስ መረጃ እንደሚያመለክተው ኢራን ውስጥ ኢንተርኔት ከተቋረጠ 37ተኛ ቀኑን ይዟል። ባለፉት ከ964 ሰዓት በላይ ለሚሆን ጊዜም ኢራናውያን ከውጭው ዓለም ተቆራርጠዋል።

    በኢራን ከውጭ ዓለም ጋር የሚደረግ የኢንተርኔት ግንኙነት በመደበኛው ሁኔታ ሊኖር ከሚገባው አንድ በመቶ ብቻ ሆኖ ቀጥሏል።

    ኔትብሎክስ እንደገለጸው፤ በአሁኑ ሰዓት የኢራን የኢንተርኔት መቋረጥ "በየትኛውም አገር ከተመዘገቡት አገር አቀፍ የኢንተርኔት መዘጋቶች ሁሉ እጅግ ረጅሙ” ሆኖ ተመዝግቧል። በኢራን ያለው የኢንተርኔት ሁኔታ “ከዚህ ቀደም ከተመዘገቡ ተመሳሳይ ክስተቶች ሁሉ የከፋ ነው" ብሏል።

    ይሁን እንጂ የተወሰኑ ባለሥልጣናት፣ የመንግሥት ደጋፊ የሆኑ ተጠቃሚዎች እና ጋዜጠኞች አሁንም ያልተገደበ የኢንተርኔት አቅርቦት እንዳላቸው ቢቢሲ ተረድቷል። ሌሎች ደግሞ ኢንተርኔት ለማግኘት በርካታ ገንዘብ እየከፈሉ ነው።

    የተወሰኑ ሰዎች እንደ ስታርሊንክ ያሉ እና ሌሎች ዘዴዎችን በመጠቀም የሳተላይት ኢንተርኔት ማግኘት ችለዋል። በዚህ መንገድ ኢንተርኔት ማግኘት ግን መዘዙ የከፋ ነው።

    ኢራን ውስጥ የኤሎን መስክን ስታርሊንክ መጠቀም ወይም ይዞ መገኘት እስከ ሁለት ዓመት ድረስ ያሳስራል። የአገሪቱ ባለሥልጣናት የሳተላይት ኢንተርኔት የሚጠቀሙ ሰዎች ለማደን ክትትል ያደርጋሉ።

    እንደ የኢራን መገናኛ ብዙኃን ዘገባ፤ ጦርነቱ ከተጀመረ አንስቶ “በመቶዎች” የሚቆጠሩ የስታርሊንክ የኢንተርኔት መሣሪያዎች ተይዘዋል።

  4. ኢራን የአሜሪካን ወታደር የማዳን ዘመቻ “ክሽፈት” እንደሆነ አድርጋ እያቀረበችው ነው

    የኢራን ጠቅላይ መሪ ለወታደራዊ አዛዦች መመሪያ ሲሰጡ የሚያሳይ የአደባባይ ላይ ስዕል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ኢራን ባለሥልጣናት እና መንግሥት በሚያወጧቸው መግለጫዎች፤ አሜሪካ ተመትቶ የወደቀው ተዋጊ ጄት ውስጥ የነበረውን የአየር ኃይል አባል ለማዳን ያካሄደችው ዘመቻ ውድቀት እንደሆነ አድርገው እያቀረቡት ነው።

    ዛሬ ጠዋት ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አሜሪካ "ድፍረት ከተሞላባቸው የፍለጋ እና የማዳን ዘመቻዎች መካከል አንዱ" የሆነ ተልዕኮ መፈጸሟን አስታውቀዋል። በዚህም ወታደሯን ማዳኗን ገልጸዋል።

    የኢራን ጦር ኻታም አል አንቢያ ማዕከል ዋና መሥሪያ ቤት ቃል አቀባይ ግን ተልዕኮውን የከሸፈ እንደሆነ አድርገው ገልጸውታል።

    “ጠላት ተመትቶ የወደቀውን ተዋጊ አብራሪውን ለመታደግ በተስፋ መቁረጥ ያካሄደው ጥረት በሁሉን ቻዩ ፈጣሪ ባርኮት እና መለኮታዊ እገዛ እንዲሁም ጊዜውን በጠበቀ እርምጃ እና የጋራ ዘመቻ ከሽፏል” ብለዋል።

    የመታደግ ተልዕኮው በሚካሄድበት ወቅት በአሜሪካ እና ኢራን ወታደሮች መካከል ውጊያ ተከፍቶ እንደነበር ተዘግቧል።

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ግን ትራምፕ "የደረሰባቸውን ከባድ ሽንፈት ለመሸፈን ሲሉ ኢራን ውስጥ የወደቀውን አውሮፕላን አብራሪ ለማዳን ልዩ ኦፕሬሽን እንደተደረገ አስመስለው [በማህበራዊ ሚዲያ] ልጥፋቸው አስፍረዋል" ብሏል።

    የኢራን መንግሥት ቴሌቪዥን ጣቢያም በዘገባዎቹ በሙሉ ተመሳሳይ ትርክት ሲያስተጋባ ነበር። ሁኔታውንም በአውሮፓውያኑ 1980 በማዕከላዊ ኢራን ታባስ ውስጥ አሜሪካዊ ታጋችን ለማዳን ተደካሄዶ ከከሸፈው ‘ኦፕሬሽን ኤግል ክላው’ ጋር በማመሳሰል አቅርቦታል።

  5. ሁለት የአሜሪካ አውሮፕላኖች ኢራን ውስጥ መውደማቸው ተዘገበ

    የአውሮፕላኖች ስብርባሪ

    የፎቶው ባለመብት, SNN

    አሜሪካዊውን የአየር ኃይል አባል ለማዳን በተካሄደው ዘመቻ ውስጥ ተሳታፊ የነበሩ ሁለት የአሜሪካ የትራንስፖርት አውሮፕላኖች መውደማቸውን ኒው ዮርክ ታይምስ ዘገበ።

    ጠፍቶ የነበረውን አሜሪካዊ ከኢራን ለማስወጣት “በመቶዎች የሚቆጠሩ የልዩ ኃይል አባላት” ተሰማርተው የነበረ ሲሆን ከኢራን ኃይሎች ጋር የተኩስ ልውውጥ ተደርጓል።

    ጋዜጣው አንድ የአሜሪካ ወታደራዊ ባለሥልጣንን ጠቅሶ እንደዘገበው “ኮማንዶዎቹን እና ፓይለቱን ከኢራን ለማስወጣት የተሰማሩት ወታደራዊ ማጓጓዣ አውሮፕላኖች ኢራን ውስጥ ባሉበት ቀርተዋል”።

    ይህንንም ተከትሎ “ከተልዕኮው በኋላ የአሜሪካ ወታደሮች ከፓይለቱ ጋር በሌሎች ሦስት አውሮፕላኖች” እንዲወጡ መደረጋቸውን እና መንቀሳቀስ ያልቻሉት የትራንስፖርት አውሮፕላኖች በኢራናውያን እጅ እንዳይገቡ በሚል እዲወድሙ መደረጋቸውን ባለሥልጣኑ ተናግረዋል።

    አንድ የኢራን የመረጃ ምንጭ እንዳስታወቀው አንድ ሲ-130 የአሜሪካ አውሮፕላን ኢስፋሃን ከተባለው የአገሪቱ ክፍል በስተደቡብ በኢራን የፖሊስ ኮማንዶ ክፍል ተመትቶ ወድቋል።

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ባወጣው መግለጫ አሜሪካ ተመትቶ የወደቀ ፓይለቷን ለማዳን አውሮፕላኖችን ባሰማራችበት ጊዜ የአገሪቱ የተለያዩ ወታደራዊ ክፍሎች በቅንጀት በወሰዱት እርምጃ “የጠላት አውሮፕላን ወድሟል፤ አሜሪካ በድጋሚ ውደርትን ተከናንባለች” ብሏል።

    የኢራን ጦር፤ ተመትቶ የወደቀውን የኤፍ-15 አውሮፕላን አባል ለማዳን አሜሪካ ባካሄደችው ዘመቻ ወቅት “ብላክ ሃውክ ሄሊኮፕተር እና ሲ-130 ወደታራዊ የትራንስፖርት አውሮፕላንን ጨምሮ የጠላት ወራሪ አውሮፕላኖች ተመትተዋል” በማለት ሁለት የአሜሪካ አየር ኃይል በራሪዎች ላይ ጥቃት መፈጸሙን አስታውቋል።

  6. አሜሪካዊው አብራሪ በኢራን ኃይሎች እንዳይያዝ ሲአይኤ አሳሳች ዘመቻ ከፍቶ እንደነበር ተዘገበ

    የአሜሪካ ኤፍ-15ኢ ተዋጊ ጄት

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    አርብ ዕለት በኢራን ሲበርር የተመታው የአሜሪካ ተዋጊ ጄት ውስጥ የነበረውን የአየር ኃይል አባል ለመታደግ ጥረት በሚደረግበት ወቅት የአሜሪካው የስለላ መስሪያ ቤት ሲአይኤ ኢራንን የሚያሳስቱ መረጃዎች ሲያሰራጭ እንደነበር ተዘገበ።

    በአሜሪካ የቢቢሲ አጋር የሆነው የሲቢኤስ ኒውስ ያወጣው ዘገባ እንደሚያሳየው በማዳን ዘመቻ ውስጥ ሲአይሴ ከፍተኛ ተሳትፎ አድርጓል። የተዋጊ ጄቱ የመሣሪያ ስርዓት መኮንን የሆነው ኮሎኔል ያለበት ቦታ ከመታወቁ አስቀድሞ ሲአይኤ ግለሰቡ እንደተገኘ እና ከአገሪቱ እያስወጡት እንደሆነ የሚገልጽ መረጃ አሰራጭቶ ነበር።

    ይህ የማሳሳቻ ዘመቻ እየተካሄደ ሳለም ተቋሙ ያሉትን አቅሞች በመጠቀም የአየር ኃይል አባሉ የሚገኝበትን ተራራማ ቦታ ማግኘት እንደቻለ አንድ ባለሥልጣን እንደነገሩት ሲቢኤስ ዘግቧል።

    ከዚያም ተቋሙ የወታደሩን ትክክለኛ አድራሻ ለአሜሪካ መከላከያ ሚኒስቴር እና ለዋይት ውስ ሰጥቷል ተብሏል። ይህ መረጃ የደረሳቸው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕም ወዲያውኑ የነፍስ አድን ዘመቻ እንዲጀመር ትዕዛዝ የሰጡ ሲሆን ሲአይኤም ከአብራሪው ጋር የተያያዙ የቀጥታ መረጃዎችን ሲያቀርብ ነበር።

    ትራምፕ ዛሬ በትሩዝ ሶሻል ማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሁፍ፤ “በሰጠሁት ትዕዛዝ መሰረት የአሜሪካ ጦር በዓለም ላይ እጅግ ገዳይ የሆኑ መሣሪያዎችን የታጣቁ በርካታ አውሮፕላኖችን ልኳል” ብለው ነበር። ፕሬዝዳንቱ የአብራሪውን መገኘት ባስታወቁበት በዚህ ልጥፋቸው ወታደሩ ጉዳት ቢደርስበትም ደህና እንደሚሆን ገልጸዋል።

    እንደ ሲቢኤስ ኒውስ ዘገባ፤ በኤፍ-15ኢ ሁለተኛ መቀመጫ ላይ የነበረው የመሣሪያ ስርዓት ባለሙያ የተጎዳው ጄቱ ከተመታ በኋላ ወደላይ ተስፈንጥሮ በሚወጣበት ወቅት ነው።

    ኮሎኔል እንደሆነ የተገለጸው ይህ ወታደር ከኢራን ኃይሎች ለማምለጥ ከአንድ ቀን በላይ ለሚሆን ጊዜ ሲጓዝ እንደነበረም ተገልጿል። የአሜሪካ ጦር በበኩሉ የኢራን ወታደሮች ወደ ስፍራው እንዳይደርሱ ቦንብ ሲጥል እና ሲተኩስ ነበር ተብሏል።

    በማዳን ዘመቻው ወቅት ጥቅም ላይ ከዋሉት አምስት የአሜሪካ ትራንስፖርት አውሮፕላኖች ውስጥ ሁለቱ ከኢራን መውጣት እንዳልቻሉ ተዘግቧል። በኢራን እንዳይያዙ ሲባልም እንዲወድሙ እንደተደረገ ተገልጿል።

  7. አሜሪካ እና ኢራን አንዳቸው በሌላኛቸው ላይ “ሲኦልን” እንደሚያመጡ ዛቱ

    እስራኤል እና አሜሪካ ቅዳሜ ዕለት በፈጸሟቸው ድብደባዎች ጉዳት ከደረሰባቸው ስፍራዎች አንዱ በቴህራን የሚገኘው ሻህዲድ ቤሄሽቲ ዩኒቨርሲቲ የምርምር ሕንጻ ነው

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, እስራኤል እና አሜሪካ ቅዳሜ ዕለት በፈጸሟቸው ድብደባዎች ጉዳት ከደረሰባቸው ስፍራዎች አንዱ በቴህራን የሚገኘው ሻህዲድ ቤሄሽቲ ዩኒቨርሲቲ የምርምር ሕንጻ ነው

    የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ለ10 ቀናት አራዝመውት የነበረው ቀነ ገደብ እየተጠናቀቀ መሆኑን ተከትሎ ኢራን ስምምነት ላይ የማትደርስ ከሆነ አገሪቱ ላይ “ሲኦልን እንደሚያዘንቡ” አስጠነቀቁ።

    የኢራን ጦር ከፍተኛ ወታደራዊ አዛዥ የሆኑት ጄነራል አሊ አብዶላሂ አሊአባዲ በበኩላቸው የትራምፕ ንግግር በመጥቀስ “የሲኦል ደጆች ይከፈቱላችኋል” ብለዋል።

    አሜሪካ እና ኢራን አንዳቸው ወደሌላኛቸው ዛቻ የሰነዘሩት ሁለቱም የጠፋውን አሜሪካው የአየር ኃይል ባልደረባ እያፈላለጉ ሳለ ነው። አሁን የአብራሪው መገኘቱን ፕሬዝዳንት ትራምፕ አስታውቀዋል።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ከዚህ አስቀድሞ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሑፍ፤ ኢራን “ስምምነት ላይ እንድትደርስ” የሰጡት የተጨማሪ 10 ቀናት ሲጠናቀቅ የአገሪቱ ኃይል ማመንጫዎች ላይ ጥቃት እንደሚፈጽሙ በድጋሚ ዝተዋል።

    ኢራን በ48 ሰዓታት ውስጥ ስምምነት ላይ ለመድረስ ካልቻለች ወይም የሆርሙዝ ወሽመጥን ካልከፈተች “ሲኦል ይወርድባቸዋል” ብለዋል።

    ትራምፕ የሰጡትን ቀነ ገደብ ውድቅ ያደረገችው ኢራን ግን ዛቻውን አጣጥላለች። የኢራን ማዕከላዊ ዕዝ አዛዥ የሆኑት ጄነራል አሊአባዲ፤ የትራምፕን ዛቻ “የረዳት አልባነት፣ የድንጋጤ፣ ሚዛኑን የሳተ እና የሞኝነት ተግባር" ሲሉ ጠርተውታል።

    የኢራን ጦር ማዕከላዊ ዋና መሥሪያ ቤት ኻታም አል አንቢያ ቃል አቀባይ ኢብራሂም ዞልፋጋሪ በበኩላቸው “ጠብ ጫሪነቱ የሚቀጥል ከሆነ መላ ቀጣናው ሲኦል ይሆልናችኋል። የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክን የማሸነፍ ቅዠት፤ የምትሰምጡበት አዘቅት ይሆናል” ሲሉ ዝተዋል።

    አሜሪካ እና እስራኤል የኢራንን ወታደራዊ፣ የኤነርጂ እና ሌሎች የኢንዱስትሩ ስፍራዎች መደብደብ ቀጥለዋል።

    ኩዌት ደግሞ በኢራን ድሮኖች በተፈጸመ ጥቃት ሁለት ኃይል ማመንጫ ጣቢያዎች እና ውሃን ከጨው ማጣሪያ ስፍራ መመታታቸውን አስታውቃለች።

  8. የጠፋው የአሜሪካ አየር ኃይል አባል በነበረበት ስፍራ በተፈጸሙ ጥቃቶች አራት ሰዎች መገደላቸው ተገለጸ

    የአሜሪካ አውሮፕላኖች በፍለጋ ላይ

    የጠፋውን የአየር ኃይል አባል ለመታደግ የተንቀሳቀሱ የአሜሪካ ኃይሎች ነበሩበት በተባለ የኢራን አካባቢ በተፈጸሙ ጥቃቶች አራት ሰዎች መደገላቸውን የአገሪቱ መንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘገበ።

    የኢራን እስላማዊ እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ በበኩሉ አሜሪካዊውን አብራሪ ሲፈልጉ የነበሩ ድሮኖችን መትቶ መጣሉን አስታውቋል።

    ከአብዮታዊ ዘቡ ጋር ግንኙነት ያለው ታስኒም የዜና ወኪል ሰዎች ስለመገደላቸው ዘገባ ያወጣው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አብራሪውን መታደግ መቻሉን ከማረጋገጣቸው አስቀድሞ ነው።

    በዘገባው ላይ የተጠቀሱት የአካባቢው ባለሥልጣን በተራራማው ኮህጊሉዬህ እና ቦየር አህማድ ግዛት ውስጥ በተፈጸሙ ጥቃቶች ቢያንስ ሦስት ሰዎች ተገድለዋል። የግዛቱ ገዢ ለተፈጸመው ጥቃት ተጠያቂ ያደረጉት አሜሪካ እና እስራኤልን ነው።

    ከዚህ በኋላ በወጣ ዘገባ ላይ ደግሞ ምክትል ገዢው ፋታህ ሞሐማዲ የሟቾች ቁጥር ወደ አራት ከፍ ማለቱን ለመገናኛ ብዙኃኑ ተናግረዋል።

    እነዚህ ጥቃቶች አሜሪካ ኢራን ውስጥ ተዋጊ ጄት ሲያበርር የተመታውን አብራሪዋን ለመታደግ ካካሄደቸው ዘመቻ ጋር ይገናኝ እንደሆን ግልጽ አይደለም።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ አብራሪውን ለማዳን በርካታ አውሮፕላኖች ተሰማርተው እንደነበር ገልጸዋል። የኢራን አብዮታዊ ዘብ ፍለጋ ላይ የነበሩ የአሜሪካ ድሮኖችን መትቶ መጣሉን እንደገለጸ የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘግቧል።

    ከፊል ይፋዊ የሆነው ፋርስ የዜና ወኪል እንደዘገበው በኢታን ደቡባዊ ኢስፋሃን ግዛት ውስጥ የአሜሪካ ድሮን ተከስክሷል። ስለዚህ ክስተት ከአሜሪካ በኩል ማረጋገጫ አልተሰጠም።

  9. አሜሪካ ኢራን ውስጥ ተዋጊ ጄት ሲያበር የተመታውን አብራሪዋን ታደገች

    የአሜሪካ  ኤፍ-15ኢ ስትራይክ ኤግል ተዋጊ ጄት

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    አርብ ዕለት በደቡባዊ ኢራን ተመትቶ የወደቀውን የአሜሪካ ተዋጊ ጄት ውስጥ የነበረው የአየር ኃይል አባል መገኘቱን ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አስታወቁ።

    የአሜሪካ ኤፍ-15ኢ ስትራይክ ኤግል ተዋጊ ጄት ኢራን ግዛት ውስጥ ከተመታ በኋላ ሁለቱም አገራት አብራሪዎቹን ሲያድኑ ነበር።

    አሜሪካ በዚያው ቀን አንዱን አብራሪ መታደግ የቻለች ሲሆን ሁለተኛውን የአየር ኃይል አባል ለማዳን በጠላት ግዛት ውስጥ አደገኛ የፍለጋ ዘመቻ ስታከናውን ነበር።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ዛሬ በትሩዝ ሶሻል ማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሑፍ “አግኝተነዋል” ሲሉ ሁለተኛውን አብራሪ መታደግ መቻሉን አስታውቀዋል። ጠፍቶ የነበረው የአየር ኃይል ባልደረባ “ጉዳት ቢደርስበትም” በጥሩ ሁኔታ ላይ እንደሚገኝ ገልጸዋል።

    “ላለፉት በርካታ ሰዓታት የአሜሪካ ሠራዊት ከአሜሪካ ታሪክ ውስጥ እጅግ ድፍረት የተሞላበትን የፍለጋ እና የማዳን ዘመቻ አካሂዷል” ብለዋል።

    የጠፋው የአየር ኃይል አባል “እጅግ የተከበረ ኮሎኔል” ሲሉ የገለጹት ትራምፕ፤ “በኢራን አደገኛ ተራሮች ውስጥ ከጠላት መስመር ጀርባ ሆኖ፣ በጠላቶቻችን እየታደነ” ነበር ብለዋል።

    ይሁን እንጂ የአሜሪካ ኃይሎች “በቀን ለ24 ሰዓታት ያለበትን ቦታ ሲከታተሉ እንደነበር” ጠቅሰዋል። “ጉዳት ደርሶበታል፤ ነገር ግን ደህና ይሆናል” ብለዋል።

    ትራምፕ በዚህ ልጥፋቸው እስካሁን ድረስ ከአስተዳደራቸው ይፋዊ ማረጋገጫ ስላልተሰጠበት የመጀመሪያው አብራሪም አንስተዋል።

    የመጀመሪያውን “ጀግና አብራሪ” መታደግ ስለመቻሉ ማረጋገጫ ያልተሰጠው “ሁለተኛውን የመታደግ ዘመቻ እያዳያበላሽ” በሚል እንደሆነ አስረድተዋል።

    “መቼም ቢሆን አሜሪካዊ ተዋጊን አንተውም” ሲሉም አክለዋል። እንደ ትራምፕ ገለጻ በኢራን ግዛት ውስጥ የማዳን ዘመቻ የተከናወነው “አንድም አሜሪካዊ ሳይገደል ወይም ሳይጎዳ” ነው።

    “የጠላት መስመር” ውስጥ የነበረውን አሜሪካዊ ወታደር ለመታደግ “በርካታ አውሮፕላኖች” ተሰማርተው እንደነበረም ተናግረዋል።

    አሜሪካ መታደግ የቻለችው አብራሪዋ በኢራን ባለሥልጣናትም ፍለጋ ሲካሄድበት ነበር። የኢራን ጦር አሜሪካዊውን ወታደር ለያዘ ሰው ከ66 ሺህ ዶላር በላይ ሽልማት ማዘጋጀቱን አስታውቆ ነበር።

    ማኅበራዊ ሚዲያ ላይ የተለቀቁ ቪዲዮዎችም በመቶዎች የሚቆጠሩ ኢራናውያን በደቡብ ምዕራባዊ ኢራን ወደሚገኘው ተራራማ ቦታ ሲያመሩ አሳይተዋል።

  10. ባህሬን የኢራን ጦርነት ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ 450 ድሮኖችን ማክሸፏን አስታወቀች

    የኢራን ጦርነት የካቲት 21 2018 ዓ.ም. ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ ባሕሬን ተደጋጋሚ የሚሳዔል እና የድሮን ጥቃቶችን አስተናግዳለች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የኢራን ጦርነት የካቲት 21 2018 ዓ.ም. ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ ባሕሬን ተደጋጋሚ የሚሳዔል እና የድሮን ጥቃቶችን አስተናግዳለች

    ባሕሬን የኢራን ጦርነት ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ ምን ያህል የአየር ጥቃቶችን ማክሸፏን ዛሬ ይፋ አድርጋለች።

    በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ ይፋ በሆነው መረጃ መሠረት ጦርነቱ ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ ከኢራን የተወነጨፈ 188 ሚሳዔሎችን እና 453 የድሮን ጥቃቶች “ማክሸፏን እና ማውደሟን” አስታውቃለች።

    የዩናይትድ አረብ ኤሜሬትስ መከላከያ ሚኒስቴር በበኩሉ በዛሬው ዕለት ብቻ 56 ድሮኖችን እና 23 ባለስቲክ ሚሳዔሎችን ማክሸፏን አስታውቋል።

    ከአምስት ሳምንት በፊት ጦርነቱ ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ 498 ባሌስቲክ ሚሳዔሎችን እና 23 ክሩዝ ሚሳዔሎችን እንዲሁም 2ሺህ 141 ድሮኖችን ማክሸፉን ሚኒስቴሩ በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ ባጋራው መረጃ ላይ ይፋ አድርጓል።

    ጦርነቱ ከተጀመረ ጊዜ አንስቶም ሁለት የአገሪቱ ጦር አባላት፣ አንድ የውጭ አገር ባለሙያ እና 10 ዜጎች መገደላቸው ተገልጿል።

    217 ሰዎች ደግሞ ጉዳት ደርሶባቸዋል።

    በጦርነቱ የመጀመሪያዎቹ ሦስት ሳምንታት ውስጥ ስለ ኢራን ጥቃቶች የዘገቡ መገናኛ ብዙኃን ይፋ ያደረጉት መረጃ እንደሚያሳየው የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ ከፍተኛ ዒላማ ሆና ቆይታለች።

  11. ላለፉት 36 ቀናት ያለ ኢንተርኔት ያሳለፉት ኢራናውያን

    ኔትብሎክስ

    የፎቶው ባለመብት, Netblocks

    በኢራን ኢንተርኔት ከተቋረጠ እና አብዛኛው ተጠቃሚ ከቀሪው ዓለም ከተቆራረጠ 36ኛ ቀኑን ይዟል።

    የዓለም የኢንተርኔት ግንኙነትን የሚቆጣጠረው ኔትብሎክስ በኢራን ኢንተርኔት ከተቋረጠ ከ840 በላይ ሰዓታት ማለፉን አስታውቋል።

    ኔትብሎክስ በኢራን የኢንተርኔት ግንኙነት ከዚህ ቀደም ከነበረው 1 በመቶ ላይ ይገኛል ብሏል።

    ቢቢሲ የተወሰኑ የአገሪቱ ባለሥልጣናት፣ የመንግሥት ደጋፊ ተቋማት እና ጋዜጠኞች ያልተገደበ የኢንተርኔት አገልግሎት እንደሚያገኙ መረዳት ችሏል።

    በኢራን ውስን ሰዎች እንደ ስታርሊንክ ያሉ ሳተላይቶች በመጠቀም የኢንተርኔት አገልግሎት ያገኛሉ። ነገር ግን ክፍያው ውድ ነው።

    በኢራን ስታርሊንክ ሲጠቀሙ የተገኙ ግለሰቦች እስከ ሁለት ዓመት በሚደርስ እስራት ይቀጣሉ።

    የኢራን መገናኛ ብዙኃን ጦርነቱ ከተጀመረ ጊዜ ጀምሮ “በመቶዎች” የሚቆጠሩ የስታርሊንክ መሣሪያዎች መያዛቸውን ዘግበዋል።

  12. የአሜሪካ እና እስራኤል ጥቃት ዒላማ የሆኑት የኢራን ዩኒቨርስቲዎች

    የኢራን ዩኒቨርስቲዎች እና ሳይንሳዊ የምርምር ማዕከሎች የአሜሪካ እና እስራኤል ጦር ተደጋጋሚ ጥቃትን አስተናግደዋል።

    የኢራን ሳይንስ ሚኒስቴር ቢያንስ 30 የአገሪቱ ዩኒቨርስቲዎች ጦርነቱ ከተጀመረ ጀምሮ በተፈጸመባቸው ጥቃት መውደማቸውን አስታውቋል።

    ቴህራን የጥቃቱ ዒላማ የአገሪቱን ሳይንሳዊ እና ባሕላዊ መሠረቶች ማጥፋት ነው ስትል ትኮንናለች።

    በጦርነቱ በተደጋጋሚ ጥቃት ከደረሰባቸው ዩኒቨርስቲዎች መካከል ከምህንድስና ጋር ተያያዥነት ያላቸው ተቋማት ይገኙበታል።

    ለኢራን ኢንዱስትሪዎች እና የመከላከያ ዘርፍ ከፍተኛ አስተዋጽኦ የሚያደርጉት እነዚህ ተቋማት የአሜሪካ እና የእስራኤል ጥቃት ተደጋጋሚ ዒላማ ሆነዋል።

  13. የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የራዲዮአክቲቭ ጨረር መሹለክ በባሕረ ሰላጤው አገራት “ሕይወትን ይቀጥፋል” አሉ

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራጋቺ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራጋቺ በቡሽህር የኒውክሌር ጣቢያ አቅራቢያ የተፈጸመውን ጥቃት አስመልክተው አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።

    በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት አስተያየት "በዩክሬን በዛፖሪዥያ የኒውክሌር ኃይል ማመንጫ ጣቢያ አካባቢ ስላለው ግጭት የምዕራባውያን ቁጣን አስታውሱ? እስራኤል-አሜሪካ የቡሽህር ጣቢያ አራት ጊዜ በቦምብ ደብድበዋል።

    “ራዲዮአክቲቭ ጨረር ሾልኮ ቢወጣ በቴህራን ሳይሆን በባሕረ ሰላጤው አገራት ዋና ከተሞች ሕይወትን ይቀጥፋል" ብለዋል።

    አሜሪካም ሆነች እስራኤል በኒውክሌር ጣቢያው አቅራቢያ ጥቃት ስለመፈጸማቸው እስካሁን ድረስ ያሉት የለም።

  14. ዓለም አቀፉ የኒውክሌር ተቆጣጣሪ በኒውክሌር ኃይል ማመንጫዎች አካባቢ “ከፍተኛ ወታደራዊ ጥንቃቄ” እንዲደረግ አሳሰበ

    ዓለም አቀፉ አቶሚክ ኤነርጂ ኤጀንሲ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ዓለም አቀፉ አቶሚክ ኤነርጂ ኤጀንሲ በቡሻህር የኒውክሌር ኃይል ማመንጫ አካባቢ ስለተፈጸመው ጥቃት መረጃ እንደደረሰው ጠቅሶ “ጥልቅ ስጋት” እንደተሰማው አስታወቀ።

    ኤጀንሲው በኤክሰ ገጹ ላይ “የራዲየሽን [ጨረር] መጠን መጨመር አልተመዘገበም" ብሏል።

    አክሎም በኒውክሌር የኃይል ማመንጫ ላይ እና አካባቢዎቹ “ጥቃት መፈጸም የለበትም” ያለ ሲሆን የኒውክሌር አደጋ እንዳይፈጠር “ከፍተኛ ወታደራዊ ጥንቃቄ” እንዲደረግ ጥሪ አቅርቧል።

  15. ኢራን በኒውክሌር ኃይል ማመንጫዋ አቅራቢያ ለአራተኛ ጊዜ ጥቃት መፈፀሙን አስታወቀች

    ከግጭቱ በፊት የቡሻህር ኒውክሌር ኃይል ማመንጫ ጣቢያ የሚያሳይ የሳተላይት ምስል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ከግጭቱ በፊት የቡሻህር ኒውክሌር ኃይል ማመንጫ ጣቢያ የሚያሳይ የሳተላይት ምስል

    የኢራን አቶሚክ ኢነርጂ ድርጅት የቡሻህር የኒውክሌር ኃይል ማመንጫ አካባቢ ጦርነቱ ከተጀመረ ዛሬ ለአራተኛ ጊዜ ጥቃት እንደደረሰበት አስታወቀ።

    ድርጅቱ ከፋብሪካው የጥበቃ ሠራተኞች አንዱ በጥቃቱ መገደሉን የገለጸ ሲሆን አሜሪካንና እስራኤልን ተጠያቂ አድርጓል።

    አሜሪካ እና እስራኤል ጥቃቱ ስለመፈጸሙ አላረጋገጡም።

    መግለጫው አክሎም የተደረጉ የመጀመሪያ ደረጃ ምርመራዎች ጥቃቱ በፋብሪካው ዋና ዋና ክፍሎች ላይ "ጉዳት አላደረሰም" እንዲሁም ሥራው ላይ "ምንም ተጽእኖ አላስከተለም"።

    ሆኖም ግን የኒውክሌር ኃይል ማመንጫው "ከፍተኛ መጠን ያለው የራዲዮአክቲቭ ንጥረ ነገር" ስለያዘ ማንኛውም ከባድ ጉዳት "ትልቅ የኒውክሌር አደጋ" ሊያስከትል እንደሚችል አስጠነቅቋል።

    ቡሻህር የኢራን ብቸኛ በሥራ ላይ ያለ የኒውክሌር ኃይል ማመንጫ ሲሆን የተጠናቀቀው በሩሲያ ድጋፍ ነው።

    የጦርነቱን መጀመር ተከትሎ ሞስኮ ብዙዎቹን ሠራተኞቿን ከፋብሪካው አስወጥታለች።

    የሩሲያ የኒውክሌር ኮርፖሬሽን ኃላፊ ሮዛቶም አሌክሲ ሊካቼቭ ከሁለት ቀናት በፊት ወደ 200 የሚጠጉ ሰዎችን ያካተተ "የመጨረሻው ቡድን" ኢራንን ለቅቆ ለመውጣት በሚቀጥለው ሳምንት ቀጠሮ ተይዞለታል።

    የኢራን የኒውክሌር ፕሮግራም ለረጅም ጊዜ የክርክር ነጥብ ሆኖ ቆይቷል። ይህም ሰፊ ዓለም አቀፍ ማዕቀቦችን አስከትሏል።

  16. ስለጠፋው የአሜሪካ አየር ኃይል ባልደረባ ምን እናውቃለን?

    የአሜሪካ ተዋጊ ጄት

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የአሜሪካ ኤፍ-15ኢ ተዋጊ ጄት

    አርብ ዕለት በደቡባዊ ኢራን አንድ የአሜሪካ ኤፍ-15ኢ ተዋጊ ጄት በኢራን ሚሳዔል ተመትቶ ተከሰከሰ።

    አብራሪው በአሜሪካ ወታደሮች የተገኘ ቢሆንም በጄቱ ውስጥ የነበረው እና የጦር መሳሪያ ሥርዓት ባለመያው ግን እስካሁን እንደጠፋ ነው።

    የጠፋውን የአየር ኃይል ባልደረባ ለመፈለግ ሁለት ሄሊኮፕተሮችን እና አንድ ኤ-10 ዋርትሆግ አውሮፕላን ተሰማርተዋል።

    የጠፋውን ባልደረባ የመፈለግ ዘመቻ ላይ ከተሰማሩት ከኤፍ-15ኢ ጄት የተረፈውን አብራሪ ይዞ እየበረረ የነበረ አንድ ሄሊኮፕተር በተተኮሰበት መሣሪያ የተመታ ቢሆንም ተሳፍረው የነበሩት ላይ መጠነኛ ጉዳት ከመድረሱ በስተቀር በሰላም ማረፍ ችሏል።

    የጠፋውን የአየር ኃይል ባልደረባ የሚደረገውን ፍለጋ እያገዘ የነበረ አንድ ኤ-10 ዋርትሆግም በኢራን ሚሳዔል የተመታ ሲሆን አብራሪው በባህረ ሰላጤው ላይ ዘልሎ በመውጣት መትረፍ ችሏል።

    ኢራን መጀመሪያ የተከሰከሰውን ተዋጊ ጄት ፍለጋ ላይ ተሰማርቶ የነበረውን ኤ-10 ዋርትሆግ የአሜሪካ ጦር አውሮፕላን መትታ መጣሏን ተናግራለች።

    የኢራን ባለሥልጣናት የጠፋውን የአየር ኃይል ለሚይዙ ሰዎች የ66,100 ዶላር ሽልማት እንደሚሰጡ በአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ተናግረዋል።

    የአሜሪካ አየር ኃይል የሚያካሄደው የፍለጋ ተልዕኮ በምን ሁኔታ ላይ እንዳለ አይታወቅም። እንዲሁም ኢራን የአየር ኃይል አባሉን ስለማግኘቷ ምንም ዓይነት መረጃ የለም።

    የጠፋው የአየር ኃይል አባል በሕይወት ስለመኖሩ ወይም ኤ-10 ዋርትሆግ ኢራን ተኩሳ መጣሏን በተመለከተ የተሟላ መረጃ የለም።

  17. ኢራን በአገሪቱ ደቡባዊ ክፍል የሚገኙ ዋና የፔትሮኬሚካል ፋብሪካዎች የአየር ድብደባ እደተፈጸመባቸው አስታወቀች

    በእስራኤል ጥቃት ጉዳት የደረሰበት አካባቢ የሚታየዑየኢራን የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    በኢራን ደቡባዊ ግዛት የኩዜስታን አስተዳደር የደኅንነት ምክትል ኃላፊ የማህሻህር ፔትሮኬሚካል ፋብሪካ ዛሬ በአየር ድብደባ ጥቃት እንደተፈጸመበት ተናገሩ።

    ከቫሊዮላህ ሃያቲ በተጨማሪም የባንዳር ኢማም ፔትሮኬሚካል ኩባንያም ዒላማ ከሆኑት መካከል እንደሆነ ተናግረዋል። አሜሪካ እና እስራኤልን ሁለቱንም የኬሚካል ኢንዱስትሪዎች በማጥቃት ወንጅለዋቸዋል።

    የኢራን የዜና አውታሮች ሃያቲን ጠቅሰው እንደዘገቡት ጥቃቶቹ ከተፈጸሙ በኋላ እስካሁን አምስት ሰዎች መቁሰላቸው ታውቋል።

    ሁለቱም ተቋማት የኢራን የፔትሮኬሚካል ኢንዱስትሪ አካል ሲሆኑ ነዳጅና ጋዝን በመጠቀም ለውጭ ገበያ የሚቀርቡ ምርቶችን ያመርታሉ።

    በአገሪቱ ደቡባዊ ክፍል የሚገኙት እነዚህ ተቋማት የፔትሮኬሚካል ምርት ማዕከል ሲሆኑ ከፋርስ ባሕረ ሰላጤ ወደ ውጭ የሚላኩ ምርቶችን አምራች ናቸው።

    የፔትሮኬሚካል ልዩ የኢኮኖሚ ዞን ድርጅት ባወጣው መግለጫ በኢንዱስትሪ ዞኑ ውስጥ ያሉ ሠራተኞች ከአካባቢው እንዲወጡ ተደርገዋል።

    ጥቃቱን ተከትሎ ሊከሰቱ የሚችሉ ብክለቶችም “ለጎረቤት ከተሞች አደጋ አይፈጥሩም” ብሏል።

    የእስራኤል የመከላከያ ሠራዊት "በአጠቃላይ ስለሁኔታው አስተያየት መስጠት እንደማይችል" ለቢቢሲ ተናግሯል።

  18. የአሜሪካን አየር ኃይል አባል መያዝ ለኢራን 'ትልቅ ሽልማት' ይሆናል- አሜሪካዊ ባለሙያ

    በቻተም ሃውስ የአሜሪካ እና የሰሜን አሜሪካ ፕሮግራም ዳይሬክተር ላውረል ራፕ ከሬዲዮ 4 ቱዴይ ፕሮግራም ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ ወቅት በተከሰከሰው ጄት ውስጥ የነበረውን እና የጠፋውን የአየር ኃይል አባል ማግኘት "ወሳኝ ተልዕኮ" ነው ብለዋል።

    የአሜሪካን አየር ኃይል አባል መያዙ ለኢራን "ትልቅ ሽልማት" እንደሚሆን እና "በጣም ከፍተኛ የመደራደሪያ አቅም" እንደሚሰጣት ተናግረዋል።

    ራፕ አክለውም የአየር ኃይሉ አባል ከተያዘ እና ምስሎች ተቀርጸው ከተለቀቁ የአሜሪካ ሕዝብ ቀድሞውንም ስላልደገፈው ጦርነት የሚኖረውን አመለካከት ሊያጠለሸው ይችላል ብለዋል።

    "እነዚያ ምስሎች ከወጡ የአሜሪካዊያንን ዕይታ በእጅጉ ይቀይሩታል" ብለዋል።

    የአየር ኃይል አባሉ ከተያዘ ለኢራን የበለጠ ዕድል የሚሰጣት ሲሆን የሚኖሩ ውይይቶችም ግጭቱን ከማርገብ ይልቅ ታሳሪውን ወደ ማስለቀቅ ሊዞሩ ይችላሉ ብለዋል።

    "አሁን፤ የዚህ ዘመቻ ግቦች ግልጽ አይደሉም... የበለጠ ደግሞ ውስብስብ እየሆኑ መጥተዋል" ሲሉ አክለዋል።

  19. ኢራን መትታ የጣለቻቸው ሁለት የአሜሪካ ተዋጊ አውሮፕላኖች የፈጠሩት የፖለቲካ ራስ ምታት

    የአሜሪካ አየር ኃይል ንብረት የሆነው ኤፍ-15ኢ ስትራይክ ኢግል ተዋጊ ጄት

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የአሜሪካ አየር ኃይል ንብረት የሆነው ኤፍ-15ኢ ስትራይክ ኢግል ተዋጊ ጄት

    ቴህራን አርብ ዕለት በደቡባዊ ኢራን አካባቢ የአሜሪካን ኤፍ-15ኢ ተዋጊ ጄትን መትታ ከጣለች በኋላ አውሮፕላኑ ውስጥ የነበረን አንድ አሜሪካዊ ለማግኘት ሁለቱ አገራት የሚያደርጉት ሩጫ ቀጥሏል።

    የኤፍ-15ኢ ተዋጊ ጄት አብራሪ በአሜሪካ መገኘቱ የተገለጠ ቢሆንም የመሣሪያ ሥርዓቱን የሚቆጣጠረው ባልደረባው ግን አሁንም እንደጠፋ ነው።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ ኢራን በባሕረ ሰላጤው ላይ ሌላ የአሜሪካ ተዋጊ አውሮፕላን መትታ መጣሏን አስታውቃለች።

    የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን ኤ-10 ዋርትሆግ የተባለ አውሮፕላን መጀመርያ ተመትቶ የወደቀውን ተዋጊ ጄት ፍለጋ ላይ እያለ ተመትቶ መውደቁን ዘግበዋል።

    የዋርትሆግ አብራሪ በባሕረ ሰላጤው አካባቢ ከአውሮፕላኑ ዘሎ ከወጣ በኋላ መገኘቱን የቢቢሲ አጋር የሆነው ሲቢኤስ ዘግቧል።

    ኢራን የአሜሪካ የጦር አውሮፕላኖች ላይ ጥቃት የሰነዘረችው የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ፒት ሄግሴት አገራቸው በኢራን ሰማይ ላይ የበላይነት እንዳላት እና የቴህራንን የአየር መቃወሚያ ማንኮታኮታቸውን ከተናገሩ ከአራት ቀናት በኋላ ነው።

    ሄግሴት የአሜሪካ አየር ኃይል አሁን ዝግ ብሎ የሚበረውን ቢ-52 ቦምብ ጣይ በኢራን ሰማይ ላይ ማብረር ይችላሉ ሲሉ ተናግረው ነበር።

    አሜሪካ በኢራን ላይ የከፈተችውን ጦርነት ተከትሎ እስካሁን ድረስ 13 ወታደሮቿ ሲገደሉ 365 ደግሞ ቆስለዋል።

    የአሜሪካ ፕሬዚዳንት በኢራን ተመትቶ የወደቀው አውሮፕላን በሁለቱ አገራት መካከል የሚካሄደውን ድርድር አይጎዳውም ሲሉ ተደምጠዋል።

    ነገር ግን ይህ እየተፈለገ ያለው አሜሪካዊ በኢራን እጅ ከወደቀ በፍጥነት ይቀየራል።

    ክፉኛ ተንኮታክቷል የተባለው የኢራን አየር መቃወሚያም አሁንም ለአሜሪካ የፖለቲካ እና የጦሩ ራስ ምታት መሆኑንም አሳይቷል።

  20. በውጊያ ወቅት ተመትቶ የወደቀን የአሜሪካ ጦር አባል ፈልጎ ማዳን ሲባል ምን ማለት ነው?

    የአሜሪካ አየር ኃይል ቦይንግ ኬሲ-135 ስትራቶታንከር አየር ላይ ነዳጅ የሚሞላ አውሮፕላን ምሰል

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የምስሉ መግለጫ, የአሜሪካ አየር ኃይል ቦይንግ ኬሲ-135 ስትራቶታንከር አየር ላይ ነዳጅ የሚሞላ አውሮፕላን ምሰል ነው። እአአ በመጋቢት ወር በአሜሪካ ነዳጅ በሚሞላ አውሮፕላን ውስጥ የነበሩ ስድስት የበረራ አባላት ተገድለዋል።

    በቀላል ቋንቋ ይህ ተልዕኮ በውጊያ ወቅት ተመትቶ የወደቀን አብራሪ ወይንም በጠላት ጦር ተቆርጦ የቀረን ሠራዊት የመፈለግ፣ ድጋፍ የመስጠት እና የማትረፍ ዘመቻ ነው።

    ይህ ከተለመደው በሰብዓዊ ቀውስ ውስጥ ወይም በአደጋ ውስጥ ያሉ ሰዎችን ፈልጎ የማግኘት ጥረት በተቃራኒው ጦርነት በሚካሄድባቸው እና በአወዛጋቢ ስፍራዎች የሚካሄድ ዘመቻ ነው።

    አንዳንድ ጊዜ አርብ ዕለት በኢራን ግዛት እንደሆነው ሁሉ ፍለጋው እና በሕይወት የማግኘቱ ሥራ የሚሰራው በጠላት ግዛት ውስጥ ዘልቆ በመግባት ይሆናል።

    የፍለጋ እና በሕይወት የማትረፍ ዘመቻው የሚካሄደው በሂሊኮፕተር ሲሆን አብሮም በበረራ ላይ ነዳጅ መሙላት የሚያስችል አውሮፕላን እንዲሁም በመንገድ ላይ ከጠላት ጥቃት ቢገጥም ጥቃት የሚፈጽም እና አካባቢውን የሚቃኝ አውሮፕላን ድጋፍ ለመስጠት ይከተላሉ።

    የቀድሞ አዛዥ እና የዚህ ልዩ ኃይል አባል የነበረ ግለሰብ ለሲቢኤስ እንደተናገረው በኢራን ውስጥ እንደተካሄደው የፍለጋ እና በሕይወት የማዳን ተግባር ቢያንስ በብላክ ሆክ ሂሊኮፕተር የሚታገዙ 24 አባላት ይሳተፉበታል።

    ይህ የፍለጋ ቡድን አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ ከአውሮፕላኑ ላይ ዘሎ የሚወርድ ሲሆን መሬት ካረፈ በኋላም ከጠፋው የአውሮፕላን አብራሪ ጋር ግንኙነት መፍጠር ቀዳሚ ተግባሩ ይሆናል።

    የጠፋው የአውሮፕላን አብራሪ ከተገኘ በኋላ አስፈላጊ ከሆነ የሕክምና ድጋፍ መስጠት፣ ከጠላት ዕይታ መሰወር እና አካባቢውን ለቅቀው የሚወጡበት ስፍራ ላይ መገኘት ይኖርባቸዋል ሲል ሲቢኤስ ዘግቧል።

    የቀድሞው አዛዥ ለሲቢኤስ "አስፈሪ እና አደገኛ ማለት ሁኔታውን ማቃለል ነው" ሲል ተናግሯል።

    አክሎም "በመላው ዓለም ይህንን ለማከናወን ነው የሰለጠኑት። ስዊስ አርሚ ናይቭስ ኦፍ ዘ ኤር ፎርስ (የአየር ኃይሉ የስዊዝ ቢላ) በመባል ነው የሚታወቁት" ብሏል።

    አርብ ዕለት ኢራን ውስጥ የተቀረጸ እና ትክክለኛነቱ የተረጋገጠ ተንቀሳቃሽ ምስል የአሜሪካ ሂሊኮፕተር እና ቢያንስ አንድ ነዳጅ የሚሞላ አውሮፕላን በኢራን ኩህዜስታን አውራጃ ሰማይ ላይ ሲበሩ ታይተዋል።

    ተጨማሪ ለማንበብ ቀጣዩን መስፈንጠሪያ ይጫኑ