ቀጥታ, አሜሪካ ኢራን ውስጥ ተዋጊ ጄት ሲያበርር የተመታውን አብራሪዋን ታደገች

አርብ ዕለት በደቡባዊ ኢራን ተመትቶ የወደቀውን የአሜሪካ ተዋጊ ጄት ሲያበርሩ ከነበሩ ሁለት ሰዎች ውስጥ ሲፈለግ የነበረው የአየር ኃይል አባል መገኘቱን ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አስታወቁ። ጠፍቶ የነበረውን የአየር ኃይል አባል “እጅግ የተከበረ ኮሎኔል” ሲሉ የገለጹት ትራምፕ፤ “በኢራን አደገኛ ተራሮች ውስጥ ከጠላት መስመር ጀርባ ሆኖ፣ በጠላቶቻችን እየታደነ” ነበር ብለዋል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. አሜሪካዊው አብራሪ በኢራን ኃይሎች እንዳይያዝ ሲአይኤ አሳሳች ዘመቻ ከፍቶ እንደነበር ተዘገበ

    አርብ ዕለት በኢራን ሲበርር የተመታው የአሜሪካ ተዋጊ ጄት ውስጥ የነበረውን የአየር ኃይል አባል ለመታደግ ጥረት በሚደረግበት ወቅት የአሜሪካው የስለላ መስሪያ ቤት ሲአይኤ ኢራንን የሚያሳስቱ መረጃዎች ሲያሰራጭ እንደነበር ተዘገበ።

    በአሜሪካ የቢቢሲ አጋር የሆነው የሲቢኤስ ኒውስ ያወጣው ዘገባ እንደሚያሳየው በማዳን ዘመቻ ውስጥ ሲአይሴ ከፍተኛ ተሳትፎ አድርጓል። የተዋጊ ጄቱ የመሣሪያ ስርዓት መኮንን የሆነው ኮሎኔል ያለበት ቦታ ከመታወቁ አስቀድሞ ሲአይኤ ግለሰቡ እንደተገኘ እና ከአገሪቱ እያስወጡት እንደሆነ የሚገልጽ መረጃ አሰራጭቶ ነበር።

    ይህ የማሳሳቻ ዘመቻ እየተካሄደ ሳለም ተቋሙ ያሉትን አቅሞች በመጠቀም የአየር ኃይል አባሉ የሚገኝበትን ተራራማ ቦታ ማግኘት እንደቻለ አንድ ባለሥልጣን እንደነገሩት ሲቢኤስ ዘግቧል።

    ከዚያም ተቋሙ የወታደሩን ትክክለኛ አድራሻ ለአሜሪካ መከላከያ ሚኒስቴር እና ለዋይት ውስ ሰጥቷል ተብሏል። ይህ መረጃ የደረሳቸው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕም ወዲያውኑ የነፍስ አድን ዘመቻ እንዲጀመር ትዕዛዝ የሰጡ ሲሆን ሲአይኤም ከአብራሪው ጋር የተያያዙ የቀጥታ መረጃዎችን ሲያቀርብ ነበር።

    ትራምፕ ዛሬ በትሩዝ ሶሻል ማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሁፍ፤ “በሰጠሁት ትዕዛዝ መሰረት የአሜሪካ ጦር በዓለም ላይ እጅግ ገዳይ የሆኑ መሣሪያዎችን የታጣቁ በርካታ አውሮፕላኖችን ልኳል” ብለው ነበር። ፕሬዝዳንቱ የአብራሪውን መገኘት ባስታወቁበት በዚህ ልጥፋቸው ወታደሩ ጉዳት ቢደርስበትም ደህና እንደሚሆን ገልጸዋል።

    እንደ ሲቢኤስ ኒውስ ዘገባ፤ በኤፍ-15ኢ ሁለተኛ መቀመጫ ላይ የነበረው የመሣሪያ ስርዓት ባለሙያ የተጎዳው ጄቱ ከተመታ በኋላ ወደላይ ተስፈንጥሮ በሚወጣበት ወቅት ነው።

    ኮሎኔል እንደሆነ የተገለጸው ይህ ወታደር ከኢራን ኃይሎች ለማምለጥ ከአንድ ቀን በላይ ለሚሆን ጊዜ ሲጓዝ እንደነበረም ተገልጿል። የአሜሪካ ጦር በበኩሉ የኢራን ወታደሮች ወደ ስፍራው እንዳይደርሱ ቦንብ ሲጥል እና ሲተኩስ ነበር ተብሏል።

    በማዳን ዘመቻው ወቅት ጥቅም ላይ ከዋሉት አምስት የአሜሪካ ትራንስፖርት አውሮፕላኖች ውስጥ ሁለቱ ከኢራን መውጣት እንዳልቻሉ ተዘግቧል። በኢራን እንዳይያዙ ሲባልም እንዲወድሙ እንደተደረገ ተገልጿል።

  2. አሜሪካ እና ኢራን አንዳቸው በሌላኛቸው ላይ “ሲኦልን” እንደሚያመጡ ዛቱ

    የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ለ10 ቀናት አራዝመውት የነበረው ቀነ ገደብ እየተጠናቀቀ መሆኑን ተከትሎ ኢራን ስምምነት ላይ የማትደርስ ከሆነ አገሪቱ ላይ “ሲኦልን እንደሚያዘንቡ” አስጠነቀቁ።

    የኢራን ጦር ከፍተኛ ወታደራዊ አዛዥ የሆኑት ጄነራል አሊ አብዶላሂ አሊአባዲ በበኩላቸው የትራምፕ ንግግር በመጥቀስ “የሲኦል ደጆች ይከፈቱላችኋል” ብለዋል።

    አሜሪካ እና ኢራን አንዳቸው ወደሌላኛቸው ዛቻ የሰነዘሩት ሁለቱም የጠፋውን አሜሪካው የአየር ኃይል ባልደረባ እያፈላለጉ ሳለ ነው። አሁን የአብራሪው መገኘቱን ፕሬዝዳንት ትራምፕ አስታውቀዋል።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ከዚህ አስቀድሞ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሑፍ፤ ኢራን “ስምምነት ላይ እንድትደርስ” የሰጡት የተጨማሪ 10 ቀናት ሲጠናቀቅ የአገሪቱ ኃይል ማመንጫዎች ላይ ጥቃት እንደሚፈጽሙ በድጋሚ ዝተዋል።

    ኢራን በ48 ሰዓታት ውስጥ ስምምነት ላይ ለመድረስ ካልቻለች ወይም የሆርሙዝ ወሽመጥን ካልከፈተች “ሲኦል ይወርድባቸዋል” ብለዋል።

    ትራምፕ የሰጡትን ቀነ ገደብ ውድቅ ያደረገችው ኢራን ግን ዛቻውን አጣጥላለች። የኢራን ማዕከላዊ ዕዝ አዛዥ የሆኑት ጄነራል አሊአባዲ፤ የትራምፕን ዛቻ “የረዳት አልባነት፣ የድንጋጤ፣ ሚዛኑን የሳተ እና የሞኝነት ተግባር" ሲሉ ጠርተውታል።

    የኢራን ጦር ማዕከላዊ ዋና መሥሪያ ቤት ኻታም አል አንቢያ ቃል አቀባይ ኢብራሂም ዞልፋጋሪ በበኩላቸው “ጠብ ጫሪነቱ የሚቀጥል ከሆነ መላ ቀጣናው ሲኦል ይሆልናችኋል። የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክን የማሸነፍ ቅዠት፤ የምትሰምጡበት አዘቅት ይሆናል” ሲሉ ዝተዋል።

    አሜሪካ እና እስራኤል የኢራንን ወታደራዊ፣ የኤነርጂ እና ሌሎች የኢንዱስትሩ ስፍራዎች መደብደብ ቀጥለዋል።

    ኩዌት ደግሞ በኢራን ድሮኖች በተፈጸመ ጥቃት ሁለት ኃይል ማመንጫ ጣቢያዎች እና ውሃን ከጨው ማጣሪያ ስፍራ መመታታቸውን አስታውቃለች።

  3. የጠፋው የአሜሪካ አየር ኃይል አባል በነበረበት ስፍራ በተፈጸሙ ጥቃቶች አራት ሰዎች መገደላቸው ተገለጸ

    የጠፋውን የአየር ኃይል አባል ለመታደግ የተንቀሳቀሱ የአሜሪካ ኃይሎች ነበሩበት በተባለ የኢራን አካባቢ በተፈጸሙ ጥቃቶች አራት ሰዎች መደገላቸውን የአገሪቱ መንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘገበ።

    የኢራን እስላማዊ እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ በበኩሉ አሜሪካዊውን አብራሪ ሲፈልጉ የነበሩ ድሮኖችን መትቶ መጣሉን አስታውቋል።

    ከአብዮታዊ ዘቡ ጋር ግንኙነት ያለው ታስኒም የዜና ወኪል ሰዎች ስለመገደላቸው ዘገባ ያወጣው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አብራሪውን መታደግ መቻሉን ከማረጋገጣቸው አስቀድሞ ነው።

    በዘገባው ላይ የተጠቀሱት የአካባቢው ባለሥልጣን በተራራማው ኮህጊሉዬህ እና ቦየር አህማድ ግዛት ውስጥ በተፈጸሙ ጥቃቶች ቢያንስ ሦስት ሰዎች ተገድለዋል። የግዛቱ ገዢ ለተፈጸመው ጥቃት ተጠያቂ ያደረጉት አሜሪካ እና እስራኤልን ነው።

    ከዚህ በኋላ በወጣ ዘገባ ላይ ደግሞ ምክትል ገዢው ፋታህ ሞሐማዲ የሟቾች ቁጥር ወደ አራት ከፍ ማለቱን ለመገናኛ ብዙኃኑ ተናግረዋል።

    እነዚህ ጥቃቶች አሜሪካ ኢራን ውስጥ ተዋጊ ጄት ሲያበርር የተመታውን አብራሪዋን ለመታደግ ካካሄደቸው ዘመቻ ጋር ይገናኝ እንደሆን ግልጽ አይደለም።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ አብራሪውን ለማዳን በርካታ አውሮፕላኖች ተሰማርተው እንደነበር ገልጸዋል። የኢራን አብዮታዊ ዘብ ፍለጋ ላይ የነበሩ የአሜሪካ ድሮኖችን መትቶ መጣሉን እንደገለጸ የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘግቧል።

    ከፊል ይፋዊ የሆነው ፋርስ የዜና ወኪል እንደዘገበው በኢታን ደቡባዊ ኢስፋሃን ግዛት ውስጥ የአሜሪካ ድሮን ተከስክሷል። ስለዚህ ክስተት ከአሜሪካ በኩል ማረጋገጫ አልተሰጠም።

  4. አሜሪካ ኢራን ውስጥ ተዋጊ ጄት ሲያበር የተመታውን አብራሪዋን ታደገች

    አርብ ዕለት በደቡባዊ ኢራን ተመትቶ የወደቀውን የአሜሪካ ተዋጊ ጄት ውስጥ የነበረው የአየር ኃይል አባል መገኘቱን ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አስታወቁ።

    የአሜሪካ ኤፍ-15ኢ ስትራይክ ኤግል ተዋጊ ጄት ኢራን ግዛት ውስጥ ከተመታ በኋላ ሁለቱም አገራት አብራሪዎቹን ሲያድኑ ነበር።

    አሜሪካ በዚያው ቀን አንዱን አብራሪ መታደግ የቻለች ሲሆን ሁለተኛውን የአየር ኃይል አባል ለማዳን በጠላት ግዛት ውስጥ አደገኛ የፍለጋ ዘመቻ ስታከናውን ነበር።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ዛሬ በትሩዝ ሶሻል ማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሑፍ “አግኝተነዋል” ሲሉ ሁለተኛውን አብራሪ መታደግ መቻሉን አስታውቀዋል። ጠፍቶ የነበረው የአየር ኃይል ባልደረባ “ጉዳት ቢደርስበትም” በጥሩ ሁኔታ ላይ እንደሚገኝ ገልጸዋል።

    “ላለፉት በርካታ ሰዓታት የአሜሪካ ሠራዊት ከአሜሪካ ታሪክ ውስጥ እጅግ ድፍረት የተሞላበትን የፍለጋ እና የማዳን ዘመቻ አካሂዷል” ብለዋል።

    የጠፋው የአየር ኃይል አባል “እጅግ የተከበረ ኮሎኔል” ሲሉ የገለጹት ትራምፕ፤ “በኢራን አደገኛ ተራሮች ውስጥ ከጠላት መስመር ጀርባ ሆኖ፣ በጠላቶቻችን እየታደነ” ነበር ብለዋል።

    ይሁን እንጂ የአሜሪካ ኃይሎች “በቀን ለ24 ሰዓታት ያለበትን ቦታ ሲከታተሉ እንደነበር” ጠቅሰዋል። “ጉዳት ደርሶበታል፤ ነገር ግን ደህና ይሆናል” ብለዋል።

    ትራምፕ በዚህ ልጥፋቸው እስካሁን ድረስ ከአስተዳደራቸው ይፋዊ ማረጋገጫ ስላልተሰጠበት የመጀመሪያው አብራሪም አንስተዋል።

    የመጀመሪያውን “ጀግና አብራሪ” መታደግ ስለመቻሉ ማረጋገጫ ያልተሰጠው “ሁለተኛውን የመታደግ ዘመቻ እያዳያበላሽ” በሚል እንደሆነ አስረድተዋል።

    “መቼም ቢሆን አሜሪካዊ ተዋጊን አንተውም” ሲሉም አክለዋል። እንደ ትራምፕ ገለጻ በኢራን ግዛት ውስጥ የማዳን ዘመቻ የተከናወነው “አንድም አሜሪካዊ ሳይገደል ወይም ሳይጎዳ” ነው።

    “የጠላት መስመር” ውስጥ የነበረውን አሜሪካዊ ወታደር ለመታደግ “በርካታ አውሮፕላኖች” ተሰማርተው እንደነበረም ተናግረዋል።

    አሜሪካ መታደግ የቻለችው አብራሪዋ በኢራን ባለሥልጣናትም ፍለጋ ሲካሄድበት ነበር። የኢራን ጦር አሜሪካዊውን ወታደር ለያዘ ሰው ከ66 ሺህ ዶላር በላይ ሽልማት ማዘጋጀቱን አስታውቆ ነበር።

    ማኅበራዊ ሚዲያ ላይ የተለቀቁ ቪዲዮዎችም በመቶዎች የሚቆጠሩ ኢራናውያን በደቡብ ምዕራባዊ ኢራን ወደሚገኘው ተራራማ ቦታ ሲያመሩ አሳይተዋል።

  5. ባህሬን የኢራን ጦርነት ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ 450 ድሮኖችን ማክሸፏን አስታወቀች

    ባሕሬን የኢራን ጦርነት ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ ምን ያህል የአየር ጥቃቶችን ማክሸፏን ዛሬ ይፋ አድርጋለች።

    በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ ይፋ በሆነው መረጃ መሠረት ጦርነቱ ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ ከኢራን የተወነጨፈ 188 ሚሳዔሎችን እና 453 የድሮን ጥቃቶች “ማክሸፏን እና ማውደሟን” አስታውቃለች።

    የዩናይትድ አረብ ኤሜሬትስ መከላከያ ሚኒስቴር በበኩሉ በዛሬው ዕለት ብቻ 56 ድሮኖችን እና 23 ባለስቲክ ሚሳዔሎችን ማክሸፏን አስታውቋል።

    ከአምስት ሳምንት በፊት ጦርነቱ ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ 498 ባሌስቲክ ሚሳዔሎችን እና 23 ክሩዝ ሚሳዔሎችን እንዲሁም 2ሺህ 141 ድሮኖችን ማክሸፉን ሚኒስቴሩ በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ ባጋራው መረጃ ላይ ይፋ አድርጓል።

    ጦርነቱ ከተጀመረ ጊዜ አንስቶም ሁለት የአገሪቱ ጦር አባላት፣ አንድ የውጭ አገር ባለሙያ እና 10 ዜጎች መገደላቸው ተገልጿል።

    217 ሰዎች ደግሞ ጉዳት ደርሶባቸዋል።

    በጦርነቱ የመጀመሪያዎቹ ሦስት ሳምንታት ውስጥ ስለ ኢራን ጥቃቶች የዘገቡ መገናኛ ብዙኃን ይፋ ያደረጉት መረጃ እንደሚያሳየው የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ ከፍተኛ ዒላማ ሆና ቆይታለች።

  6. ላለፉት 36 ቀናት ያለ ኢንተርኔት ያሳለፉት ኢራናውያን

    በኢራን ኢንተርኔት ከተቋረጠ እና አብዛኛው ተጠቃሚ ከቀሪው ዓለም ከተቆራረጠ 36ኛ ቀኑን ይዟል።

    የዓለም የኢንተርኔት ግንኙነትን የሚቆጣጠረው ኔትብሎክስ በኢራን ኢንተርኔት ከተቋረጠ ከ840 በላይ ሰዓታት ማለፉን አስታውቋል።

    ኔትብሎክስ በኢራን የኢንተርኔት ግንኙነት ከዚህ ቀደም ከነበረው 1 በመቶ ላይ ይገኛል ብሏል።

    ቢቢሲ የተወሰኑ የአገሪቱ ባለሥልጣናት፣ የመንግሥት ደጋፊ ተቋማት እና ጋዜጠኞች ያልተገደበ የኢንተርኔት አገልግሎት እንደሚያገኙ መረዳት ችሏል።

    በኢራን ውስን ሰዎች እንደ ስታርሊንክ ያሉ ሳተላይቶች በመጠቀም የኢንተርኔት አገልግሎት ያገኛሉ። ነገር ግን ክፍያው ውድ ነው።

    በኢራን ስታርሊንክ ሲጠቀሙ የተገኙ ግለሰቦች እስከ ሁለት ዓመት በሚደርስ እስራት ይቀጣሉ።

    የኢራን መገናኛ ብዙኃን ጦርነቱ ከተጀመረ ጊዜ ጀምሮ “በመቶዎች” የሚቆጠሩ የስታርሊንክ መሣሪያዎች መያዛቸውን ዘግበዋል።

  7. የአሜሪካ እና እስራኤል ጥቃት ዒላማ የሆኑት የኢራን ዩኒቨርስቲዎች

    የኢራን ዩኒቨርስቲዎች እና ሳይንሳዊ የምርምር ማዕከሎች የአሜሪካ እና እስራኤል ጦር ተደጋጋሚ ጥቃትን አስተናግደዋል።

    የኢራን ሳይንስ ሚኒስቴር ቢያንስ 30 የአገሪቱ ዩኒቨርስቲዎች ጦርነቱ ከተጀመረ ጀምሮ በተፈጸመባቸው ጥቃት መውደማቸውን አስታውቋል።

    ቴህራን የጥቃቱ ዒላማ የአገሪቱን ሳይንሳዊ እና ባሕላዊ መሠረቶች ማጥፋት ነው ስትል ትኮንናለች።

    በጦርነቱ በተደጋጋሚ ጥቃት ከደረሰባቸው ዩኒቨርስቲዎች መካከል ከምህንድስና ጋር ተያያዥነት ያላቸው ተቋማት ይገኙበታል።

    ለኢራን ኢንዱስትሪዎች እና የመከላከያ ዘርፍ ከፍተኛ አስተዋጽኦ የሚያደርጉት እነዚህ ተቋማት የአሜሪካ እና የእስራኤል ጥቃት ተደጋጋሚ ዒላማ ሆነዋል።

  8. የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የራዲዮአክቲቭ ጨረር መሹለክ በባሕረ ሰላጤው አገራት “ሕይወትን ይቀጥፋል” አሉ

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራጋቺ በቡሽህር የኒውክሌር ጣቢያ አቅራቢያ የተፈጸመውን ጥቃት አስመልክተው አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።

    በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት አስተያየት "በዩክሬን በዛፖሪዥያ የኒውክሌር ኃይል ማመንጫ ጣቢያ አካባቢ ስላለው ግጭት የምዕራባውያን ቁጣን አስታውሱ? እስራኤል-አሜሪካ የቡሽህር ጣቢያ አራት ጊዜ በቦምብ ደብድበዋል።

    “ራዲዮአክቲቭ ጨረር ሾልኮ ቢወጣ በቴህራን ሳይሆን በባሕረ ሰላጤው አገራት ዋና ከተሞች ሕይወትን ይቀጥፋል" ብለዋል።

    አሜሪካም ሆነች እስራኤል በኒውክሌር ጣቢያው አቅራቢያ ጥቃት ስለመፈጸማቸው እስካሁን ድረስ ያሉት የለም።

  9. ዓለም አቀፉ የኒውክሌር ተቆጣጣሪ በኒውክሌር ኃይል ማመንጫዎች አካባቢ “ከፍተኛ ወታደራዊ ጥንቃቄ” እንዲደረግ አሳሰበ

    ዓለም አቀፉ አቶሚክ ኤነርጂ ኤጀንሲ በቡሻህር የኒውክሌር ኃይል ማመንጫ አካባቢ ስለተፈጸመው ጥቃት መረጃ እንደደረሰው ጠቅሶ “ጥልቅ ስጋት” እንደተሰማው አስታወቀ።

    ኤጀንሲው በኤክሰ ገጹ ላይ “የራዲየሽን [ጨረር] መጠን መጨመር አልተመዘገበም" ብሏል።

    አክሎም በኒውክሌር የኃይል ማመንጫ ላይ እና አካባቢዎቹ “ጥቃት መፈጸም የለበትም” ያለ ሲሆን የኒውክሌር አደጋ እንዳይፈጠር “ከፍተኛ ወታደራዊ ጥንቃቄ” እንዲደረግ ጥሪ አቅርቧል።

  10. ኢራን በኒውክሌር ኃይል ማመንጫዋ አቅራቢያ ለአራተኛ ጊዜ ጥቃት መፈፀሙን አስታወቀች

    የኢራን አቶሚክ ኢነርጂ ድርጅት የቡሻህር የኒውክሌር ኃይል ማመንጫ አካባቢ ጦርነቱ ከተጀመረ ዛሬ ለአራተኛ ጊዜ ጥቃት እንደደረሰበት አስታወቀ።

    ድርጅቱ ከፋብሪካው የጥበቃ ሠራተኞች አንዱ በጥቃቱ መገደሉን የገለጸ ሲሆን አሜሪካንና እስራኤልን ተጠያቂ አድርጓል።

    አሜሪካ እና እስራኤል ጥቃቱ ስለመፈጸሙ አላረጋገጡም።

    መግለጫው አክሎም የተደረጉ የመጀመሪያ ደረጃ ምርመራዎች ጥቃቱ በፋብሪካው ዋና ዋና ክፍሎች ላይ "ጉዳት አላደረሰም" እንዲሁም ሥራው ላይ "ምንም ተጽእኖ አላስከተለም"።

    ሆኖም ግን የኒውክሌር ኃይል ማመንጫው "ከፍተኛ መጠን ያለው የራዲዮአክቲቭ ንጥረ ነገር" ስለያዘ ማንኛውም ከባድ ጉዳት "ትልቅ የኒውክሌር አደጋ" ሊያስከትል እንደሚችል አስጠነቅቋል።

    ቡሻህር የኢራን ብቸኛ በሥራ ላይ ያለ የኒውክሌር ኃይል ማመንጫ ሲሆን የተጠናቀቀው በሩሲያ ድጋፍ ነው።

    የጦርነቱን መጀመር ተከትሎ ሞስኮ ብዙዎቹን ሠራተኞቿን ከፋብሪካው አስወጥታለች።

    የሩሲያ የኒውክሌር ኮርፖሬሽን ኃላፊ ሮዛቶም አሌክሲ ሊካቼቭ ከሁለት ቀናት በፊት ወደ 200 የሚጠጉ ሰዎችን ያካተተ "የመጨረሻው ቡድን" ኢራንን ለቅቆ ለመውጣት በሚቀጥለው ሳምንት ቀጠሮ ተይዞለታል።

    የኢራን የኒውክሌር ፕሮግራም ለረጅም ጊዜ የክርክር ነጥብ ሆኖ ቆይቷል። ይህም ሰፊ ዓለም አቀፍ ማዕቀቦችን አስከትሏል።

  11. ስለጠፋው የአሜሪካ አየር ኃይል ባልደረባ ምን እናውቃለን?

    አርብ ዕለት በደቡባዊ ኢራን አንድ የአሜሪካ ኤፍ-15ኢ ተዋጊ ጄት በኢራን ሚሳዔል ተመትቶ ተከሰከሰ።

    አብራሪው በአሜሪካ ወታደሮች የተገኘ ቢሆንም በጄቱ ውስጥ የነበረው እና የጦር መሳሪያ ሥርዓት ባለመያው ግን እስካሁን እንደጠፋ ነው።

    የጠፋውን የአየር ኃይል ባልደረባ ለመፈለግ ሁለት ሄሊኮፕተሮችን እና አንድ ኤ-10 ዋርትሆግ አውሮፕላን ተሰማርተዋል።

    የጠፋውን ባልደረባ የመፈለግ ዘመቻ ላይ ከተሰማሩት ከኤፍ-15ኢ ጄት የተረፈውን አብራሪ ይዞ እየበረረ የነበረ አንድ ሄሊኮፕተር በተተኮሰበት መሣሪያ የተመታ ቢሆንም ተሳፍረው የነበሩት ላይ መጠነኛ ጉዳት ከመድረሱ በስተቀር በሰላም ማረፍ ችሏል።

    የጠፋውን የአየር ኃይል ባልደረባ የሚደረገውን ፍለጋ እያገዘ የነበረ አንድ ኤ-10 ዋርትሆግም በኢራን ሚሳዔል የተመታ ሲሆን አብራሪው በባህረ ሰላጤው ላይ ዘልሎ በመውጣት መትረፍ ችሏል።

    ኢራን መጀመሪያ የተከሰከሰውን ተዋጊ ጄት ፍለጋ ላይ ተሰማርቶ የነበረውን ኤ-10 ዋርትሆግ የአሜሪካ ጦር አውሮፕላን መትታ መጣሏን ተናግራለች።

    የኢራን ባለሥልጣናት የጠፋውን የአየር ኃይል ለሚይዙ ሰዎች የ66,100 ዶላር ሽልማት እንደሚሰጡ በአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ተናግረዋል።

    የአሜሪካ አየር ኃይል የሚያካሄደው የፍለጋ ተልዕኮ በምን ሁኔታ ላይ እንዳለ አይታወቅም። እንዲሁም ኢራን የአየር ኃይል አባሉን ስለማግኘቷ ምንም ዓይነት መረጃ የለም።

    የጠፋው የአየር ኃይል አባል በሕይወት ስለመኖሩ ወይም ኤ-10 ዋርትሆግ ኢራን ተኩሳ መጣሏን በተመለከተ የተሟላ መረጃ የለም።

  12. ኢራን በአገሪቱ ደቡባዊ ክፍል የሚገኙ ዋና የፔትሮኬሚካል ፋብሪካዎች የአየር ድብደባ እደተፈጸመባቸው አስታወቀች

    በኢራን ደቡባዊ ግዛት የኩዜስታን አስተዳደር የደኅንነት ምክትል ኃላፊ የማህሻህር ፔትሮኬሚካል ፋብሪካ ዛሬ በአየር ድብደባ ጥቃት እንደተፈጸመበት ተናገሩ።

    ከቫሊዮላህ ሃያቲ በተጨማሪም የባንዳር ኢማም ፔትሮኬሚካል ኩባንያም ዒላማ ከሆኑት መካከል እንደሆነ ተናግረዋል። አሜሪካ እና እስራኤልን ሁለቱንም የኬሚካል ኢንዱስትሪዎች በማጥቃት ወንጅለዋቸዋል።

    የኢራን የዜና አውታሮች ሃያቲን ጠቅሰው እንደዘገቡት ጥቃቶቹ ከተፈጸሙ በኋላ እስካሁን አምስት ሰዎች መቁሰላቸው ታውቋል።

    ሁለቱም ተቋማት የኢራን የፔትሮኬሚካል ኢንዱስትሪ አካል ሲሆኑ ነዳጅና ጋዝን በመጠቀም ለውጭ ገበያ የሚቀርቡ ምርቶችን ያመርታሉ።

    በአገሪቱ ደቡባዊ ክፍል የሚገኙት እነዚህ ተቋማት የፔትሮኬሚካል ምርት ማዕከል ሲሆኑ ከፋርስ ባሕረ ሰላጤ ወደ ውጭ የሚላኩ ምርቶችን አምራች ናቸው።

    የፔትሮኬሚካል ልዩ የኢኮኖሚ ዞን ድርጅት ባወጣው መግለጫ በኢንዱስትሪ ዞኑ ውስጥ ያሉ ሠራተኞች ከአካባቢው እንዲወጡ ተደርገዋል።

    ጥቃቱን ተከትሎ ሊከሰቱ የሚችሉ ብክለቶችም “ለጎረቤት ከተሞች አደጋ አይፈጥሩም” ብሏል።

    የእስራኤል የመከላከያ ሠራዊት "በአጠቃላይ ስለሁኔታው አስተያየት መስጠት እንደማይችል" ለቢቢሲ ተናግሯል።

  13. የአሜሪካን አየር ኃይል አባል መያዝ ለኢራን 'ትልቅ ሽልማት' ይሆናል- አሜሪካዊ ባለሙያ

    በቻተም ሃውስ የአሜሪካ እና የሰሜን አሜሪካ ፕሮግራም ዳይሬክተር ላውረል ራፕ ከሬዲዮ 4 ቱዴይ ፕሮግራም ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ ወቅት በተከሰከሰው ጄት ውስጥ የነበረውን እና የጠፋውን የአየር ኃይል አባል ማግኘት "ወሳኝ ተልዕኮ" ነው ብለዋል።

    የአሜሪካን አየር ኃይል አባል መያዙ ለኢራን "ትልቅ ሽልማት" እንደሚሆን እና "በጣም ከፍተኛ የመደራደሪያ አቅም" እንደሚሰጣት ተናግረዋል።

    ራፕ አክለውም የአየር ኃይሉ አባል ከተያዘ እና ምስሎች ተቀርጸው ከተለቀቁ የአሜሪካ ሕዝብ ቀድሞውንም ስላልደገፈው ጦርነት የሚኖረውን አመለካከት ሊያጠለሸው ይችላል ብለዋል።

    "እነዚያ ምስሎች ከወጡ የአሜሪካዊያንን ዕይታ በእጅጉ ይቀይሩታል" ብለዋል።

    የአየር ኃይል አባሉ ከተያዘ ለኢራን የበለጠ ዕድል የሚሰጣት ሲሆን የሚኖሩ ውይይቶችም ግጭቱን ከማርገብ ይልቅ ታሳሪውን ወደ ማስለቀቅ ሊዞሩ ይችላሉ ብለዋል።

    "አሁን፤ የዚህ ዘመቻ ግቦች ግልጽ አይደሉም... የበለጠ ደግሞ ውስብስብ እየሆኑ መጥተዋል" ሲሉ አክለዋል።

  14. ኢራን መትታ የጣለቻቸው ሁለት የአሜሪካ ተዋጊ አውሮፕላኖች የፈጠሩት የፖለቲካ ራስ ምታት

    ቴህራን አርብ ዕለት በደቡባዊ ኢራን አካባቢ የአሜሪካን ኤፍ-15ኢ ተዋጊ ጄትን መትታ ከጣለች በኋላ አውሮፕላኑ ውስጥ የነበረን አንድ አሜሪካዊ ለማግኘት ሁለቱ አገራት የሚያደርጉት ሩጫ ቀጥሏል።

    የኤፍ-15ኢ ተዋጊ ጄት አብራሪ በአሜሪካ መገኘቱ የተገለጠ ቢሆንም የመሣሪያ ሥርዓቱን የሚቆጣጠረው ባልደረባው ግን አሁንም እንደጠፋ ነው።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ ኢራን በባሕረ ሰላጤው ላይ ሌላ የአሜሪካ ተዋጊ አውሮፕላን መትታ መጣሏን አስታውቃለች።

    የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን ኤ-10 ዋርትሆግ የተባለ አውሮፕላን መጀመርያ ተመትቶ የወደቀውን ተዋጊ ጄት ፍለጋ ላይ እያለ ተመትቶ መውደቁን ዘግበዋል።

    የዋርትሆግ አብራሪ በባሕረ ሰላጤው አካባቢ ከአውሮፕላኑ ዘሎ ከወጣ በኋላ መገኘቱን የቢቢሲ አጋር የሆነው ሲቢኤስ ዘግቧል።

    ኢራን የአሜሪካ የጦር አውሮፕላኖች ላይ ጥቃት የሰነዘረችው የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ፒት ሄግሴት አገራቸው በኢራን ሰማይ ላይ የበላይነት እንዳላት እና የቴህራንን የአየር መቃወሚያ ማንኮታኮታቸውን ከተናገሩ ከአራት ቀናት በኋላ ነው።

    ሄግሴት የአሜሪካ አየር ኃይል አሁን ዝግ ብሎ የሚበረውን ቢ-52 ቦምብ ጣይ በኢራን ሰማይ ላይ ማብረር ይችላሉ ሲሉ ተናግረው ነበር።

    አሜሪካ በኢራን ላይ የከፈተችውን ጦርነት ተከትሎ እስካሁን ድረስ 13 ወታደሮቿ ሲገደሉ 365 ደግሞ ቆስለዋል።

    የአሜሪካ ፕሬዚዳንት በኢራን ተመትቶ የወደቀው አውሮፕላን በሁለቱ አገራት መካከል የሚካሄደውን ድርድር አይጎዳውም ሲሉ ተደምጠዋል።

    ነገር ግን ይህ እየተፈለገ ያለው አሜሪካዊ በኢራን እጅ ከወደቀ በፍጥነት ይቀየራል።

    ክፉኛ ተንኮታክቷል የተባለው የኢራን አየር መቃወሚያም አሁንም ለአሜሪካ የፖለቲካ እና የጦሩ ራስ ምታት መሆኑንም አሳይቷል።

  15. በውጊያ ወቅት ተመትቶ የወደቀን የአሜሪካ ጦር አባል ፈልጎ ማዳን ሲባል ምን ማለት ነው?

    በቀላል ቋንቋ ይህ ተልዕኮ በውጊያ ወቅት ተመትቶ የወደቀን አብራሪ ወይንም በጠላት ጦር ተቆርጦ የቀረን ሠራዊት የመፈለግ፣ ድጋፍ የመስጠት እና የማትረፍ ዘመቻ ነው።

    ይህ ከተለመደው በሰብዓዊ ቀውስ ውስጥ ወይም በአደጋ ውስጥ ያሉ ሰዎችን ፈልጎ የማግኘት ጥረት በተቃራኒው ጦርነት በሚካሄድባቸው እና በአወዛጋቢ ስፍራዎች የሚካሄድ ዘመቻ ነው።

    አንዳንድ ጊዜ አርብ ዕለት በኢራን ግዛት እንደሆነው ሁሉ ፍለጋው እና በሕይወት የማግኘቱ ሥራ የሚሰራው በጠላት ግዛት ውስጥ ዘልቆ በመግባት ይሆናል።

    የፍለጋ እና በሕይወት የማትረፍ ዘመቻው የሚካሄደው በሂሊኮፕተር ሲሆን አብሮም በበረራ ላይ ነዳጅ መሙላት የሚያስችል አውሮፕላን እንዲሁም በመንገድ ላይ ከጠላት ጥቃት ቢገጥም ጥቃት የሚፈጽም እና አካባቢውን የሚቃኝ አውሮፕላን ድጋፍ ለመስጠት ይከተላሉ።

    የቀድሞ አዛዥ እና የዚህ ልዩ ኃይል አባል የነበረ ግለሰብ ለሲቢኤስ እንደተናገረው በኢራን ውስጥ እንደተካሄደው የፍለጋ እና በሕይወት የማዳን ተግባር ቢያንስ በብላክ ሆክ ሂሊኮፕተር የሚታገዙ 24 አባላት ይሳተፉበታል።

    ይህ የፍለጋ ቡድን አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ ከአውሮፕላኑ ላይ ዘሎ የሚወርድ ሲሆን መሬት ካረፈ በኋላም ከጠፋው የአውሮፕላን አብራሪ ጋር ግንኙነት መፍጠር ቀዳሚ ተግባሩ ይሆናል።

    የጠፋው የአውሮፕላን አብራሪ ከተገኘ በኋላ አስፈላጊ ከሆነ የሕክምና ድጋፍ መስጠት፣ ከጠላት ዕይታ መሰወር እና አካባቢውን ለቅቀው የሚወጡበት ስፍራ ላይ መገኘት ይኖርባቸዋል ሲል ሲቢኤስ ዘግቧል።

    የቀድሞው አዛዥ ለሲቢኤስ "አስፈሪ እና አደገኛ ማለት ሁኔታውን ማቃለል ነው" ሲል ተናግሯል።

    አክሎም "በመላው ዓለም ይህንን ለማከናወን ነው የሰለጠኑት። ስዊስ አርሚ ናይቭስ ኦፍ ዘ ኤር ፎርስ (የአየር ኃይሉ የስዊዝ ቢላ) በመባል ነው የሚታወቁት" ብሏል።

    አርብ ዕለት ኢራን ውስጥ የተቀረጸ እና ትክክለኛነቱ የተረጋገጠ ተንቀሳቃሽ ምስል የአሜሪካ ሂሊኮፕተር እና ቢያንስ አንድ ነዳጅ የሚሞላ አውሮፕላን በኢራን ኩህዜስታን አውራጃ ሰማይ ላይ ሲበሩ ታይተዋል።

    ተጨማሪ ለማንበብ ቀጣዩን መስፈንጠሪያ ይጫኑ

  16. የኢራን ጦርነት ከተጀመረ አንስቶ ከ350 በላይ የአሜሪካ ጦር አባላት ጉዳት ደርሶባቸዋል- ፔንታጎን

    አሜሪካ እና እስራኤል በጋራ በመሆን ኢራን ላይ ጦርነት ከከፈቱበት ዕለት አንስቶ 365 የአሜሪካ ወታደሮች ጉዳት እንደደረሰባቸው ፔንታጎን አስታወቀ።

    አሜሪካ በዚህ ጦርነት ውስጥ 13 ወታደሮቿ ተገድለውባታል።

    ጉዳት የደረሰባቸው የአሜሪካ ወታደሮች ከእግረኛ፣ ባሕር ኃይል እንዲሁም ከአየር ኃይል አባላቱ የተውጣጡ መሆናቸውን የፔንታጎን መረጃ ያሳያል።

  17. ኢራን እና አሜሪካ በኢራን ግዛት ተመትቶ የወደቀውን የአየር ኃይል ባልደረባ ለማግኘት ጥድፊያ ላይ መሆናቸው ተዘገበ

    የአሜሪካ ተዋጊ ጄት በኢራን ግዛት ውስጥ ተመትቶ መውደቁ ከተሰማ በኋላ የኢራን መገናኛ ብዙኃን ከበረራ አባላቱ መካከል አንዱ በአገሪቱ ደቡባዊ ክፍል ሳያርፍ እንዳልቀረ እየዘገቡ ነው።

    የአሜሪካ ባለሥልጣናት የቢቢሲ አጋር ለሆነው ሲቢኤስ አብራሪው መገኘቱን እና አብሮት የነበረው የጦር መሣሪያ ስርዓት ተቆጣጣሪ ባልደረባው ግን እየተፈለገ መሆኑን ተናግረዋል።

    የኢራን ብሔራዊ መገናኛ ብዙኃን ዜጎች “አብራሪውን በሕይወት ይዞ ለሚያስረክብ” ዳጎስ ያለ የገንዘብ ሽልማት እንደሰጠው ሲያስተዋውቁ ተደምጠዋል።

    ሽልማቱ እስከ 66 ሺህ 100 የአሜሪካ ዶላር እንደሚደርስ የመገናኛ ብዙኃኑ ሲናገሩ ተደምጠዋል። ይህ ገንዘብ በአገሪቱ ከሚታወቀው ወርሃዊ ደሞዝ አንጻር እጅግ በጣም ከፍተኛው ነው።

    ከዚህ መግለጫ በኋላ የታጠቁ ግለሰቦች በሁለት የአገሪቱ ደቡባዊ ግዛቶች የጦር ጄቱ ውስጥ የነበሩ አባላትን ፍለጋ ላይ መሰማራታቸውን የሚያሳይ ተንቀሳቃሽ ምስል ተለቅቋል።

    አንድ ትክክለኛነቱ ያልተረጋገጠ ቪዲዮ በደቡባዊ ኩህዜስታን አውራጃ በርካታ ሰዎች ጠመንጃ እና የአገሪቱን ባንዲራ ይዘው ፍለጋ ሲሰማሩ ያሳያል። በቪዲዮው ላይ አንዱ ግለሰብ “ፈጣሪ ይረዳናል እናገኘዋለን” ሲል ይደመጣል።

  18. የአሜሪካ ጄት ኢራን ውስጥ ተመትቶ መውደቁን አሶሺዬትድ ፕሬስ ዘገበ

    የአሜሪካ ተዋጊ ጄት ኢራን ውስጥ የወደቀው ተመትቶ መሆኑን ከአሜሪካ መከላከያ ሚኒስቴር የኢሜይል መልዕክት መመልከቱን የዜና ወኪሉ አሶሺዬትድ ፕሬስ ዘገበ።

    የዜና ወኪሉ የተመለከተው የፔንታጎን ኢሜይል መካከለኛው ምሥራቅ ውስጥ “አውሮፕላን ተመትቶ ወድቋል” የሚል እንደሆነ ገልጿል። ኤሜይሉ ዝርዝር መረጃ አላከተተም ተብሏል።

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ አርብ ዕለት የአሜሪካ ተዋጊ አውሮፕላን መትቶ መጣሉን ገልጿል።

    የኢራን ባለሥልጣናት እንደሚናገሩት ጄቱ ሲመታ አብራሪው ወጥቷል፤ የአገሪቱ ዜጎችም አብራሪውን እንዲፈልጉ ጠይቀዋል።

    እንደተመታ የተገለጸው “ኤፍ-15ኢ” ተዋጊ ጄት ሁለት አብራሪዎችን የሚይዝ ሲሆን፣ የአሜሪካ ኃይሎች አንዱን እንደታደጉት ተዘግቧል።

    የአሜሪካ መንግሥት እስካሁን ድረስ ስለ ክስተቱ ይፋዊ አስተያየት አልሰጠም። ዋይት ሐውስ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ስለ ወደቀው ጄት ገለጻ እንደተደረገላቸው ከመግለጽ ውጪ ተጨማሪ መረጃ አላቀረበም።

  19. የኢራኑ አፈ ጉባኤ አሜሪካ “ከአገዛዝ ለውጥ” ወደ “ፓይለቶቻችንን አፋልጉን” ተሸጋግራለች ሲሉ ተሳለቁ

    የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባኤ እና አሜሪካ ለድርድር ከምትመርጣቸው የአገሪቱ ባለሥልጣናት መካከል አንዱ የሆኑት ሞሐማድ ባግሄር ጋሊባፍ ኢራን ውስጥ ተመትቶ መውደቁ በተዘገበው የአሜሪካ ተዋጊ ጄት ላይ ተሳለቁ።

    አፈ ጉባኤው በኤክስ ማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ አሜሪካኖች በኢራን ውስጥ የአገዛዝ ለውጥ ከማምጣት ወደ አብራሪዎቻቸውን ወደ መፈለግ መሸጋገራቸውን በምጸት ጽፈዋል።

    “በተከታታይ ኢራንን ለ37 ጊዜ ካሸነፉ በኋላ፣ ይህ ያለ ስትራቴጂ የጀመሩት ጦርነት አሁን ‘ከአገዛዝ ለውጥ’ ወደ ‘እባካችሁ ፓይለቶቻችንን አፋልጉን’ ወደሚል ደረጃ ወርዷል” ብለዋል ጋሊባፍ።

    ከቀናት በፊት ትራምፕ በኢራን ውስጥ የአገዛዝ ለውጥ መካሄዱን አፈ ጉባኤው የሚካተቱበት አዲሱ የኢራን መሪዎች ትውልድ ከቀደሙት “በጣሙን የተለሳለሱ ጽንፈኞች” እና “ምክንያታዊ” ናቸው ብለው ነበር።

    ሞሐማድ ባግሄር ጋሊባፍ በኤክስ ላይ ጨምረውም “የሚደንቅ ነው። ምን ዓይነት ለውጥ ነው። ፍጹም ብልሆች” ሲሉ በአሜሪካኖች ተሳልቀዋል።

    አንዳንድ ያልተረጋገጡ ዘገባዎች እንደሚያመለክቱት የፕሬዝዳንት ትራምፕ አስተዳደር ጋሊባፍን ቀጣይ አጋር እና ቀጣዩ የኢራን መሪ ሊሆኑ ይችላሉ ብሎ ያምናል።

  20. የወደቀውን የአሜሪካ ተዋጊ ጄት አንድ አብራሪ መታደግ መቻሉን ባለሥልጣናት ተናገሩ

    ኢራን ውስጥ የወደቀው የአሜሪካ ተዋጊ ጄት ውስጥ ከነበሩ ሁለት የአየር ኃይል አባላት መካከል አንዱን መታደግ እንደተቻለ የዋሽንግተን ባለሥልጣናት መናገራቸው ተዘገበ።

    በአሜሪካ የቢቢሲ አጋር የሆነው ሲቢኤስ ኒውስ ሁለት ባለሥልጣናትን ጠቅሶ ባወጣው ዘገባ እንዳመለከተው የወደቀው “ኤፍ-15ኢ” ተዋጊ ጄት ሁለት ሰዎችን ይዞ ነበር።

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ በአገሪቱ ማዕከላዊ ክፍል በሚገኝ አካባቢ የአሜሪካ ተዋጊ ጄትን መትቶ መጣሉን አስታውቋል።

    ማኅበራዊ ሚዲያ ላይ የወጣ እና ቢቢሲ ያረጋገጠው አንዲ ቪዲዮ አንድ የአሜሪካ አውሮፕላን በሁለት ሄሊኮፕተሮች ታጅቦ በደቡባዊ ኢራን የፍለጋ እና የመታደግ ዘመቻ ሲያካሂድ ይታያል።

    በደቡባዊ ኢራን የሚገኘው ኮህጊሉዬህ እና ቦየር አህመድ ግዛት አስተዳዳሪ፤ የተመታውን የአሜሪካ ጄት አብራሪ “በሕይወት መያዝ” ቅድሚያ የሚሰጠው ጉዳይ መሆኑን ተናግረዋል።

    “የጠላት ኃይልን መያዝ ወይም መግደል የተሳካላቸው ሰዎች በተለየ ሁኔታ በአስተዳደሩ ጽህፈት ቤት ይመሰገናሉ” ማለታቸውን የኢራን መገናኛ ብዙኃን ዘግቧል።