አሜሪካዊው አብራሪ በኢራን ኃይሎች እንዳይያዝ ሲአይኤ አሳሳች ዘመቻ ከፍቶ እንደነበር ተዘገበ
አርብ ዕለት በኢራን ሲበርር የተመታው የአሜሪካ ተዋጊ ጄት ውስጥ የነበረውን የአየር ኃይል አባል ለመታደግ ጥረት በሚደረግበት ወቅት የአሜሪካው የስለላ መስሪያ ቤት ሲአይኤ ኢራንን የሚያሳስቱ መረጃዎች ሲያሰራጭ እንደነበር ተዘገበ።
በአሜሪካ የቢቢሲ አጋር የሆነው የሲቢኤስ ኒውስ ያወጣው ዘገባ እንደሚያሳየው በማዳን ዘመቻ ውስጥ ሲአይሴ ከፍተኛ ተሳትፎ አድርጓል። የተዋጊ ጄቱ የመሣሪያ ስርዓት መኮንን የሆነው ኮሎኔል ያለበት ቦታ ከመታወቁ አስቀድሞ ሲአይኤ ግለሰቡ እንደተገኘ እና ከአገሪቱ እያስወጡት እንደሆነ የሚገልጽ መረጃ አሰራጭቶ ነበር።
ይህ የማሳሳቻ ዘመቻ እየተካሄደ ሳለም ተቋሙ ያሉትን አቅሞች በመጠቀም የአየር ኃይል አባሉ የሚገኝበትን ተራራማ ቦታ ማግኘት እንደቻለ አንድ ባለሥልጣን እንደነገሩት ሲቢኤስ ዘግቧል።
ከዚያም ተቋሙ የወታደሩን ትክክለኛ አድራሻ ለአሜሪካ መከላከያ ሚኒስቴር እና ለዋይት ውስ ሰጥቷል ተብሏል። ይህ መረጃ የደረሳቸው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕም ወዲያውኑ የነፍስ አድን ዘመቻ እንዲጀመር ትዕዛዝ የሰጡ ሲሆን ሲአይኤም ከአብራሪው ጋር የተያያዙ የቀጥታ መረጃዎችን ሲያቀርብ ነበር።
ትራምፕ ዛሬ በትሩዝ ሶሻል ማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሁፍ፤ “በሰጠሁት ትዕዛዝ መሰረት የአሜሪካ ጦር በዓለም ላይ እጅግ ገዳይ የሆኑ መሣሪያዎችን የታጣቁ በርካታ አውሮፕላኖችን ልኳል” ብለው ነበር። ፕሬዝዳንቱ የአብራሪውን መገኘት ባስታወቁበት በዚህ ልጥፋቸው ወታደሩ ጉዳት ቢደርስበትም ደህና እንደሚሆን ገልጸዋል።
እንደ ሲቢኤስ ኒውስ ዘገባ፤ በኤፍ-15ኢ ሁለተኛ መቀመጫ ላይ የነበረው የመሣሪያ ስርዓት ባለሙያ የተጎዳው ጄቱ ከተመታ በኋላ ወደላይ ተስፈንጥሮ በሚወጣበት ወቅት ነው።
ኮሎኔል እንደሆነ የተገለጸው ይህ ወታደር ከኢራን ኃይሎች ለማምለጥ ከአንድ ቀን በላይ ለሚሆን ጊዜ ሲጓዝ እንደነበረም ተገልጿል። የአሜሪካ ጦር በበኩሉ የኢራን ወታደሮች ወደ ስፍራው እንዳይደርሱ ቦንብ ሲጥል እና ሲተኩስ ነበር ተብሏል።
በማዳን ዘመቻው ወቅት ጥቅም ላይ ከዋሉት አምስት የአሜሪካ ትራንስፖርት አውሮፕላኖች ውስጥ ሁለቱ ከኢራን መውጣት እንዳልቻሉ ተዘግቧል። በኢራን እንዳይያዙ ሲባልም እንዲወድሙ እንደተደረገ ተገልጿል።