ቀጥታ, ኢራን እና አሜሪካ በኢራን ግዛት ተመትቶ የወደቀው የአየር ኃይል ባልደረባ ለማግኘት ፍለጋ ላይ መሆናቸው ተዘገበ

በኢራን ላይ ጥቃት ለመፈጸም ተሰማርቶ የነበረ የአሜሪካ ተዋጊ አውሮፕላን ተመትቶ መውደቁን እና አብራሪውን መገኘቱ ከተዘገበ በኋላ አብሮት የነበረውን ረዳቱን ለማግኘት ጥረት ቀጥሏል። የኢራን መንግሥት ግለሰቡን አግኝቶ ለሚያስረክብ ዳጎስ ያለ ገንዘብ ለመሸለም ቃል ገብቷል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ባህሬን የኢራን ጦርነት ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ 450 ድሮኖችን ማክሸፏን አስታወቀች

    ባሕሬን የኢራን ጦርነት ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ ምን ያህል የአየር ጥቃቶችን ማክሸፏን ዛሬ ይፋ አድርጋለች።

    በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ ይፋ በሆነው መረጃ መሠረት ጦርነቱ ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ ከኢራን የተወነጨፈ 188 ሚሳዔሎችን እና 453 የድሮን ጥቃቶች “ማክሸፏን እና ማውደሟን” አስታውቃለች።

    የዩናይትድ አረብ ኤሜሬትስ መከላከያ ሚኒስቴር በበኩሉ በዛሬው ዕለት ብቻ 56 ድሮኖችን እና 23 ባለስቲክ ሚሳዔሎችን ማክሸፏን አስታውቋል።

    ከአምስት ሳምንት በፊት ጦርነቱ ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ 498 ባሌስቲክ ሚሳዔሎችን እና 23 ክሩዝ ሚሳዔሎችን እንዲሁም 2ሺህ 141 ድሮኖችን ማክሸፉን ሚኒስቴሩ በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ ባጋራው መረጃ ላይ ይፋ አድርጓል።

    ጦርነቱ ከተጀመረ ጊዜ አንስቶም ሁለት የአገሪቱ ጦር አባላት፣ አንድ የውጭ አገር ባለሙያ እና 10 ዜጎች መገደላቸው ተገልጿል።

    217 ሰዎች ደግሞ ጉዳት ደርሶባቸዋል።

    በጦርነቱ የመጀመሪያዎቹ ሦስት ሳምንታት ውስጥ ስለ ኢራን ጥቃቶች የዘገቡ መገናኛ ብዙኃን ይፋ ያደረጉት መረጃ እንደሚያሳየው የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ ከፍተኛ ዒላማ ሆና ቆይታለች።

  2. ላለፉት 36 ቀናት ያለ ኢንተርኔት ያሳለፉት ኢራናውያን

    በኢራን ኢንተርኔት ከተቋረጠ እና አብዛኛው ተጠቃሚ ከቀሪው ዓለም ከተቆራረጠ 36ኛ ቀኑን ይዟል።

    የዓለም የኢንተርኔት ግንኙነትን የሚቆጣጠረው ኔትብሎክስ በኢራን ኢንተርኔት ከተቋረጠ ከ840 በላይ ሰዓታት ማለፉን አስታውቋል።

    ኔትብሎክስ በኢራን የኢንተርኔት ግንኙነት ከዚህ ቀደም ከነበረው 1 በመቶ ላይ ይገኛል ብሏል።

    ቢቢሲ የተወሰኑ የአገሪቱ ባለሥልጣናት፣ የመንግሥት ደጋፊ ተቋማት እና ጋዜጠኞች ያልተገደበ የኢንተርኔት አገልግሎት እንደሚያገኙ መረዳት ችሏል።

    በኢራን ውስን ሰዎች እንደ ስታርሊንክ ያሉ ሳተላይቶች በመጠቀም የኢንተርኔት አገልግሎት ያገኛሉ። ነገር ግን ክፍያው ውድ ነው።

    በኢራን ስታርሊንክ ሲጠቀሙ የተገኙ ግለሰቦች እስከ ሁለት ዓመት በሚደርስ እስራት ይቀጣሉ።

    የኢራን መገናኛ ብዙኃን ጦርነቱ ከተጀመረ ጊዜ ጀምሮ “በመቶዎች” የሚቆጠሩ የስታርሊንክ መሣሪያዎች መያዛቸውን ዘግበዋል።

  3. የአሜሪካ እና እስራኤል ጥቃት ዒላማ የሆኑት የኢራን ዩኒቨርስቲዎች

    የኢራን ዩኒቨርስቲዎች እና ሳይንሳዊ የምርምር ማዕከሎች የአሜሪካ እና እስራኤል ጦር ተደጋጋሚ ጥቃትን አስተናግደዋል።

    የኢራን ሳይንስ ሚኒስቴር ቢያንስ 30 የአገሪቱ ዩኒቨርስቲዎች ጦርነቱ ከተጀመረ ጀምሮ በተፈጸመባቸው ጥቃት መውደማቸውን አስታውቋል።

    ቴህራን የጥቃቱ ዒላማ የአገሪቱን ሳይንሳዊ እና ባሕላዊ መሠረቶች ማጥፋት ነው ስትል ትኮንናለች።

    በጦርነቱ በተደጋጋሚ ጥቃት ከደረሰባቸው ዩኒቨርስቲዎች መካከል ከምህንድስና ጋር ተያያዥነት ያላቸው ተቋማት ይገኙበታል።

    ለኢራን ኢንዱስትሪዎች እና የመከላከያ ዘርፍ ከፍተኛ አስተዋጽኦ የሚያደርጉት እነዚህ ተቋማት የአሜሪካ እና የእስራኤል ጥቃት ተደጋጋሚ ዒላማ ሆነዋል።

  4. የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የራዲዮአክቲቭ ጨረር መሹለክ በባሕረ ሰላጤው አገራት “ሕይወትን ይቀጥፋል” አሉ

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራጋቺ በቡሽህር የኒውክሌር ጣቢያ አቅራቢያ የተፈጸመውን ጥቃት አስመልክተው አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።

    በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት አስተያየት "በዩክሬን በዛፖሪዥያ የኒውክሌር ኃይል ማመንጫ ጣቢያ አካባቢ ስላለው ግጭት የምዕራባውያን ቁጣን አስታውሱ? እስራኤል-አሜሪካ የቡሽህር ጣቢያ አራት ጊዜ በቦምብ ደብድበዋል።

    “ራዲዮአክቲቭ ጨረር ሾልኮ ቢወጣ በቴህራን ሳይሆን በባሕረ ሰላጤው አገራት ዋና ከተሞች ሕይወትን ይቀጥፋል" ብለዋል።

    አሜሪካም ሆነች እስራኤል በኒውክሌር ጣቢያው አቅራቢያ ጥቃት ስለመፈጸማቸው እስካሁን ድረስ ያሉት የለም።

  5. ዓለም አቀፉ የኒውክሌር ተቆጣጣሪ በኒውክሌር ኃይል ማመንጫዎች አካባቢ “ከፍተኛ ወታደራዊ ጥንቃቄ” እንዲደረግ አሳሰበ

    ዓለም አቀፉ አቶሚክ ኤነርጂ ኤጀንሲ በቡሻህር የኒውክሌር ኃይል ማመንጫ አካባቢ ስለተፈጸመው ጥቃት መረጃ እንደደረሰው ጠቅሶ “ጥልቅ ስጋት” እንደተሰማው አስታወቀ።

    ኤጀንሲው በኤክሰ ገጹ ላይ “የራዲየሽን [ጨረር] መጠን መጨመር አልተመዘገበም" ብሏል።

    አክሎም በኒውክሌር የኃይል ማመንጫ ላይ እና አካባቢዎቹ “ጥቃት መፈጸም የለበትም” ያለ ሲሆን የኒውክሌር አደጋ እንዳይፈጠር “ከፍተኛ ወታደራዊ ጥንቃቄ” እንዲደረግ ጥሪ አቅርቧል።

  6. ኢራን በኒውክሌር ኃይል ማመንጫዋ አቅራቢያ ለአራተኛ ጊዜ ጥቃት መፈፀሙን አስታወቀች

    የኢራን አቶሚክ ኢነርጂ ድርጅት የቡሻህር የኒውክሌር ኃይል ማመንጫ አካባቢ ጦርነቱ ከተጀመረ ዛሬ ለአራተኛ ጊዜ ጥቃት እንደደረሰበት አስታወቀ።

    ድርጅቱ ከፋብሪካው የጥበቃ ሠራተኞች አንዱ በጥቃቱ መገደሉን የገለጸ ሲሆን አሜሪካንና እስራኤልን ተጠያቂ አድርጓል።

    አሜሪካ እና እስራኤል ጥቃቱ ስለመፈጸሙ አላረጋገጡም።

    መግለጫው አክሎም የተደረጉ የመጀመሪያ ደረጃ ምርመራዎች ጥቃቱ በፋብሪካው ዋና ዋና ክፍሎች ላይ "ጉዳት አላደረሰም" እንዲሁም ሥራው ላይ "ምንም ተጽእኖ አላስከተለም"።

    ሆኖም ግን የኒውክሌር ኃይል ማመንጫው "ከፍተኛ መጠን ያለው የራዲዮአክቲቭ ንጥረ ነገር" ስለያዘ ማንኛውም ከባድ ጉዳት "ትልቅ የኒውክሌር አደጋ" ሊያስከትል እንደሚችል አስጠነቅቋል።

    ቡሻህር የኢራን ብቸኛ በሥራ ላይ ያለ የኒውክሌር ኃይል ማመንጫ ሲሆን የተጠናቀቀው በሩሲያ ድጋፍ ነው።

    የጦርነቱን መጀመር ተከትሎ ሞስኮ ብዙዎቹን ሠራተኞቿን ከፋብሪካው አስወጥታለች።

    የሩሲያ የኒውክሌር ኮርፖሬሽን ኃላፊ ሮዛቶም አሌክሲ ሊካቼቭ ከሁለት ቀናት በፊት ወደ 200 የሚጠጉ ሰዎችን ያካተተ "የመጨረሻው ቡድን" ኢራንን ለቅቆ ለመውጣት በሚቀጥለው ሳምንት ቀጠሮ ተይዞለታል።

    የኢራን የኒውክሌር ፕሮግራም ለረጅም ጊዜ የክርክር ነጥብ ሆኖ ቆይቷል። ይህም ሰፊ ዓለም አቀፍ ማዕቀቦችን አስከትሏል።

  7. ስለጠፋው የአሜሪካ አየር ኃይል ባልደረባ ምን እናውቃለን?

    አርብ ዕለት በደቡባዊ ኢራን አንድ የአሜሪካ ኤፍ-15ኢ ተዋጊ ጄት በኢራን ሚሳዔል ተመትቶ ተከሰከሰ።

    አብራሪው በአሜሪካ ወታደሮች የተገኘ ቢሆንም በጄቱ ውስጥ የነበረው እና የጦር መሳሪያ ሥርዓት ባለመያው ግን እስካሁን እንደጠፋ ነው።

    የጠፋውን የአየር ኃይል ባልደረባ ለመፈለግ ሁለት ሄሊኮፕተሮችን እና አንድ ኤ-10 ዋርትሆግ አውሮፕላን ተሰማርተዋል።

    የጠፋውን ባልደረባ የመፈለግ ዘመቻ ላይ ከተሰማሩት ከኤፍ-15ኢ ጄት የተረፈውን አብራሪ ይዞ እየበረረ የነበረ አንድ ሄሊኮፕተር በተተኮሰበት መሣሪያ የተመታ ቢሆንም ተሳፍረው የነበሩት ላይ መጠነኛ ጉዳት ከመድረሱ በስተቀር በሰላም ማረፍ ችሏል።

    የጠፋውን የአየር ኃይል ባልደረባ የሚደረገውን ፍለጋ እያገዘ የነበረ አንድ ኤ-10 ዋርትሆግም በኢራን ሚሳዔል የተመታ ሲሆን አብራሪው በባህረ ሰላጤው ላይ ዘልሎ በመውጣት መትረፍ ችሏል።

    ኢራን መጀመሪያ የተከሰከሰውን ተዋጊ ጄት ፍለጋ ላይ ተሰማርቶ የነበረውን ኤ-10 ዋርትሆግ የአሜሪካ ጦር አውሮፕላን መትታ መጣሏን ተናግራለች።

    የኢራን ባለሥልጣናት የጠፋውን የአየር ኃይል ለሚይዙ ሰዎች የ66,100 ዶላር ሽልማት እንደሚሰጡ በአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ተናግረዋል።

    የአሜሪካ አየር ኃይል የሚያካሄደው የፍለጋ ተልዕኮ በምን ሁኔታ ላይ እንዳለ አይታወቅም። እንዲሁም ኢራን የአየር ኃይል አባሉን ስለማግኘቷ ምንም ዓይነት መረጃ የለም።

    የጠፋው የአየር ኃይል አባል በሕይወት ስለመኖሩ ወይም ኤ-10 ዋርትሆግ ኢራን ተኩሳ መጣሏን በተመለከተ የተሟላ መረጃ የለም።

  8. ኢራን በአገሪቱ ደቡባዊ ክፍል የሚገኙ ዋና የፔትሮኬሚካል ፋብሪካዎች የአየር ድብደባ እደተፈጸመባቸው አስታወቀች

    በኢራን ደቡባዊ ግዛት የኩዜስታን አስተዳደር የደኅንነት ምክትል ኃላፊ የማህሻህር ፔትሮኬሚካል ፋብሪካ ዛሬ በአየር ድብደባ ጥቃት እንደተፈጸመበት ተናገሩ።

    ከቫሊዮላህ ሃያቲ በተጨማሪም የባንዳር ኢማም ፔትሮኬሚካል ኩባንያም ዒላማ ከሆኑት መካከል እንደሆነ ተናግረዋል። አሜሪካ እና እስራኤልን ሁለቱንም የኬሚካል ኢንዱስትሪዎች በማጥቃት ወንጅለዋቸዋል።

    የኢራን የዜና አውታሮች ሃያቲን ጠቅሰው እንደዘገቡት ጥቃቶቹ ከተፈጸሙ በኋላ እስካሁን አምስት ሰዎች መቁሰላቸው ታውቋል።

    ሁለቱም ተቋማት የኢራን የፔትሮኬሚካል ኢንዱስትሪ አካል ሲሆኑ ነዳጅና ጋዝን በመጠቀም ለውጭ ገበያ የሚቀርቡ ምርቶችን ያመርታሉ።

    በአገሪቱ ደቡባዊ ክፍል የሚገኙት እነዚህ ተቋማት የፔትሮኬሚካል ምርት ማዕከል ሲሆኑ ከፋርስ ባሕረ ሰላጤ ወደ ውጭ የሚላኩ ምርቶችን አምራች ናቸው።

    የፔትሮኬሚካል ልዩ የኢኮኖሚ ዞን ድርጅት ባወጣው መግለጫ በኢንዱስትሪ ዞኑ ውስጥ ያሉ ሠራተኞች ከአካባቢው እንዲወጡ ተደርገዋል።

    ጥቃቱን ተከትሎ ሊከሰቱ የሚችሉ ብክለቶችም “ለጎረቤት ከተሞች አደጋ አይፈጥሩም” ብሏል።

    የእስራኤል የመከላከያ ሠራዊት "በአጠቃላይ ስለሁኔታው አስተያየት መስጠት እንደማይችል" ለቢቢሲ ተናግሯል።

  9. የአሜሪካን አየር ኃይል አባል መያዝ ለኢራን 'ትልቅ ሽልማት' ይሆናል- አሜሪካዊ ባለሙያ

    በቻተም ሃውስ የአሜሪካ እና የሰሜን አሜሪካ ፕሮግራም ዳይሬክተር ላውረል ራፕ ከሬዲዮ 4 ቱዴይ ፕሮግራም ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ ወቅት በተከሰከሰው ጄት ውስጥ የነበረውን እና የጠፋውን የአየር ኃይል አባል ማግኘት "ወሳኝ ተልዕኮ" ነው ብለዋል።

    የአሜሪካን አየር ኃይል አባል መያዙ ለኢራን "ትልቅ ሽልማት" እንደሚሆን እና "በጣም ከፍተኛ የመደራደሪያ አቅም" እንደሚሰጣት ተናግረዋል።

    ራፕ አክለውም የአየር ኃይሉ አባል ከተያዘ እና ምስሎች ተቀርጸው ከተለቀቁ የአሜሪካ ሕዝብ ቀድሞውንም ስላልደገፈው ጦርነት የሚኖረውን አመለካከት ሊያጠለሸው ይችላል ብለዋል።

    "እነዚያ ምስሎች ከወጡ የአሜሪካዊያንን ዕይታ በእጅጉ ይቀይሩታል" ብለዋል።

    የአየር ኃይል አባሉ ከተያዘ ለኢራን የበለጠ ዕድል የሚሰጣት ሲሆን የሚኖሩ ውይይቶችም ግጭቱን ከማርገብ ይልቅ ታሳሪውን ወደ ማስለቀቅ ሊዞሩ ይችላሉ ብለዋል።

    "አሁን፤ የዚህ ዘመቻ ግቦች ግልጽ አይደሉም... የበለጠ ደግሞ ውስብስብ እየሆኑ መጥተዋል" ሲሉ አክለዋል።

  10. ኢራን መትታ የጣለቻቸው ሁለት የአሜሪካ ተዋጊ አውሮፕላኖች የፈጠሩት የፖለቲካ ራስ ምታት

    ቴህራን አርብ ዕለት በደቡባዊ ኢራን አካባቢ የአሜሪካን ኤፍ-15ኢ ተዋጊ ጄትን መትታ ከጣለች በኋላ አውሮፕላኑ ውስጥ የነበረን አንድ አሜሪካዊ ለማግኘት ሁለቱ አገራት የሚያደርጉት ሩጫ ቀጥሏል።

    የኤፍ-15ኢ ተዋጊ ጄት አብራሪ በአሜሪካ መገኘቱ የተገለጠ ቢሆንም የመሣሪያ ሥርዓቱን የሚቆጣጠረው ባልደረባው ግን አሁንም እንደጠፋ ነው።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ ኢራን በባሕረ ሰላጤው ላይ ሌላ የአሜሪካ ተዋጊ አውሮፕላን መትታ መጣሏን አስታውቃለች።

    የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን ኤ-10 ዋርትሆግ የተባለ አውሮፕላን መጀመርያ ተመትቶ የወደቀውን ተዋጊ ጄት ፍለጋ ላይ እያለ ተመትቶ መውደቁን ዘግበዋል።

    የዋርትሆግ አብራሪ በባሕረ ሰላጤው አካባቢ ከአውሮፕላኑ ዘሎ ከወጣ በኋላ መገኘቱን የቢቢሲ አጋር የሆነው ሲቢኤስ ዘግቧል።

    ኢራን የአሜሪካ የጦር አውሮፕላኖች ላይ ጥቃት የሰነዘረችው የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ፒት ሄግሴት አገራቸው በኢራን ሰማይ ላይ የበላይነት እንዳላት እና የቴህራንን የአየር መቃወሚያ ማንኮታኮታቸውን ከተናገሩ ከአራት ቀናት በኋላ ነው።

    ሄግሴት የአሜሪካ አየር ኃይል አሁን ዝግ ብሎ የሚበረውን ቢ-52 ቦምብ ጣይ በኢራን ሰማይ ላይ ማብረር ይችላሉ ሲሉ ተናግረው ነበር።

    አሜሪካ በኢራን ላይ የከፈተችውን ጦርነት ተከትሎ እስካሁን ድረስ 13 ወታደሮቿ ሲገደሉ 365 ደግሞ ቆስለዋል።

    የአሜሪካ ፕሬዚዳንት በኢራን ተመትቶ የወደቀው አውሮፕላን በሁለቱ አገራት መካከል የሚካሄደውን ድርድር አይጎዳውም ሲሉ ተደምጠዋል።

    ነገር ግን ይህ እየተፈለገ ያለው አሜሪካዊ በኢራን እጅ ከወደቀ በፍጥነት ይቀየራል።

    ክፉኛ ተንኮታክቷል የተባለው የኢራን አየር መቃወሚያም አሁንም ለአሜሪካ የፖለቲካ እና የጦሩ ራስ ምታት መሆኑንም አሳይቷል።

  11. በውጊያ ወቅት ተመትቶ የወደቀን የአሜሪካ ጦር አባል ፈልጎ ማዳን ሲባል ምን ማለት ነው?

    በቀላል ቋንቋ ይህ ተልዕኮ በውጊያ ወቅት ተመትቶ የወደቀን አብራሪ ወይንም በጠላት ጦር ተቆርጦ የቀረን ሠራዊት የመፈለግ፣ ድጋፍ የመስጠት እና የማትረፍ ዘመቻ ነው።

    ይህ ከተለመደው በሰብዓዊ ቀውስ ውስጥ ወይም በአደጋ ውስጥ ያሉ ሰዎችን ፈልጎ የማግኘት ጥረት በተቃራኒው ጦርነት በሚካሄድባቸው እና በአወዛጋቢ ስፍራዎች የሚካሄድ ዘመቻ ነው።

    አንዳንድ ጊዜ አርብ ዕለት በኢራን ግዛት እንደሆነው ሁሉ ፍለጋው እና በሕይወት የማግኘቱ ሥራ የሚሰራው በጠላት ግዛት ውስጥ ዘልቆ በመግባት ይሆናል።

    የፍለጋ እና በሕይወት የማትረፍ ዘመቻው የሚካሄደው በሂሊኮፕተር ሲሆን አብሮም በበረራ ላይ ነዳጅ መሙላት የሚያስችል አውሮፕላን እንዲሁም በመንገድ ላይ ከጠላት ጥቃት ቢገጥም ጥቃት የሚፈጽም እና አካባቢውን የሚቃኝ አውሮፕላን ድጋፍ ለመስጠት ይከተላሉ።

    የቀድሞ አዛዥ እና የዚህ ልዩ ኃይል አባል የነበረ ግለሰብ ለሲቢኤስ እንደተናገረው በኢራን ውስጥ እንደተካሄደው የፍለጋ እና በሕይወት የማዳን ተግባር ቢያንስ በብላክ ሆክ ሂሊኮፕተር የሚታገዙ 24 አባላት ይሳተፉበታል።

    ይህ የፍለጋ ቡድን አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ ከአውሮፕላኑ ላይ ዘሎ የሚወርድ ሲሆን መሬት ካረፈ በኋላም ከጠፋው የአውሮፕላን አብራሪ ጋር ግንኙነት መፍጠር ቀዳሚ ተግባሩ ይሆናል።

    የጠፋው የአውሮፕላን አብራሪ ከተገኘ በኋላ አስፈላጊ ከሆነ የሕክምና ድጋፍ መስጠት፣ ከጠላት ዕይታ መሰወር እና አካባቢውን ለቅቀው የሚወጡበት ስፍራ ላይ መገኘት ይኖርባቸዋል ሲል ሲቢኤስ ዘግቧል።

    የቀድሞው አዛዥ ለሲቢኤስ "አስፈሪ እና አደገኛ ማለት ሁኔታውን ማቃለል ነው" ሲል ተናግሯል።

    አክሎም "በመላው ዓለም ይህንን ለማከናወን ነው የሰለጠኑት። ስዊስ አርሚ ናይቭስ ኦፍ ዘ ኤር ፎርስ (የአየር ኃይሉ የስዊዝ ቢላ) በመባል ነው የሚታወቁት" ብሏል።

    አርብ ዕለት ኢራን ውስጥ የተቀረጸ እና ትክክለኛነቱ የተረጋገጠ ተንቀሳቃሽ ምስል የአሜሪካ ሂሊኮፕተር እና ቢያንስ አንድ ነዳጅ የሚሞላ አውሮፕላን በኢራን ኩህዜስታን አውራጃ ሰማይ ላይ ሲበሩ ታይተዋል።

    ተጨማሪ ለማንበብ ቀጣዩን መስፈንጠሪያ ይጫኑ

  12. የኢራን ጦርነት ከተጀመረ አንስቶ ከ350 በላይ የአሜሪካ ጦር አባላት ጉዳት ደርሶባቸዋል- ፔንታጎን

    አሜሪካ እና እስራኤል በጋራ በመሆን ኢራን ላይ ጦርነት ከከፈቱበት ዕለት አንስቶ 365 የአሜሪካ ወታደሮች ጉዳት እንደደረሰባቸው ፔንታጎን አስታወቀ።

    አሜሪካ በዚህ ጦርነት ውስጥ 13 ወታደሮቿ ተገድለውባታል።

    ጉዳት የደረሰባቸው የአሜሪካ ወታደሮች ከእግረኛ፣ ባሕር ኃይል እንዲሁም ከአየር ኃይል አባላቱ የተውጣጡ መሆናቸውን የፔንታጎን መረጃ ያሳያል።

  13. ኢራን እና አሜሪካ በኢራን ግዛት ተመትቶ የወደቀውን የአየር ኃይል ባልደረባ ለማግኘት ጥድፊያ ላይ መሆናቸው ተዘገበ

    የአሜሪካ ተዋጊ ጄት በኢራን ግዛት ውስጥ ተመትቶ መውደቁ ከተሰማ በኋላ የኢራን መገናኛ ብዙኃን ከበረራ አባላቱ መካከል አንዱ በአገሪቱ ደቡባዊ ክፍል ሳያርፍ እንዳልቀረ እየዘገቡ ነው።

    የአሜሪካ ባለሥልጣናት የቢቢሲ አጋር ለሆነው ሲቢኤስ አብራሪው መገኘቱን እና አብሮት የነበረው የጦር መሣሪያ ስርዓት ተቆጣጣሪ ባልደረባው ግን እየተፈለገ መሆኑን ተናግረዋል።

    የኢራን ብሔራዊ መገናኛ ብዙኃን ዜጎች “አብራሪውን በሕይወት ይዞ ለሚያስረክብ” ዳጎስ ያለ የገንዘብ ሽልማት እንደሰጠው ሲያስተዋውቁ ተደምጠዋል።

    ሽልማቱ እስከ 66 ሺህ 100 የአሜሪካ ዶላር እንደሚደርስ የመገናኛ ብዙኃኑ ሲናገሩ ተደምጠዋል። ይህ ገንዘብ በአገሪቱ ከሚታወቀው ወርሃዊ ደሞዝ አንጻር እጅግ በጣም ከፍተኛው ነው።

    ከዚህ መግለጫ በኋላ የታጠቁ ግለሰቦች በሁለት የአገሪቱ ደቡባዊ ግዛቶች የጦር ጄቱ ውስጥ የነበሩ አባላትን ፍለጋ ላይ መሰማራታቸውን የሚያሳይ ተንቀሳቃሽ ምስል ተለቅቋል።

    አንድ ትክክለኛነቱ ያልተረጋገጠ ቪዲዮ በደቡባዊ ኩህዜስታን አውራጃ በርካታ ሰዎች ጠመንጃ እና የአገሪቱን ባንዲራ ይዘው ፍለጋ ሲሰማሩ ያሳያል። በቪዲዮው ላይ አንዱ ግለሰብ “ፈጣሪ ይረዳናል እናገኘዋለን” ሲል ይደመጣል።

  14. የአሜሪካ ጄት ኢራን ውስጥ ተመትቶ መውደቁን አሶሺዬትድ ፕሬስ ዘገበ

    የአሜሪካ ተዋጊ ጄት ኢራን ውስጥ የወደቀው ተመትቶ መሆኑን ከአሜሪካ መከላከያ ሚኒስቴር የኢሜይል መልዕክት መመልከቱን የዜና ወኪሉ አሶሺዬትድ ፕሬስ ዘገበ።

    የዜና ወኪሉ የተመለከተው የፔንታጎን ኢሜይል መካከለኛው ምሥራቅ ውስጥ “አውሮፕላን ተመትቶ ወድቋል” የሚል እንደሆነ ገልጿል። ኤሜይሉ ዝርዝር መረጃ አላከተተም ተብሏል።

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ አርብ ዕለት የአሜሪካ ተዋጊ አውሮፕላን መትቶ መጣሉን ገልጿል።

    የኢራን ባለሥልጣናት እንደሚናገሩት ጄቱ ሲመታ አብራሪው ወጥቷል፤ የአገሪቱ ዜጎችም አብራሪውን እንዲፈልጉ ጠይቀዋል።

    እንደተመታ የተገለጸው “ኤፍ-15ኢ” ተዋጊ ጄት ሁለት አብራሪዎችን የሚይዝ ሲሆን፣ የአሜሪካ ኃይሎች አንዱን እንደታደጉት ተዘግቧል።

    የአሜሪካ መንግሥት እስካሁን ድረስ ስለ ክስተቱ ይፋዊ አስተያየት አልሰጠም። ዋይት ሐውስ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ስለ ወደቀው ጄት ገለጻ እንደተደረገላቸው ከመግለጽ ውጪ ተጨማሪ መረጃ አላቀረበም።

  15. የኢራኑ አፈ ጉባኤ አሜሪካ “ከአገዛዝ ለውጥ” ወደ “ፓይለቶቻችንን አፋልጉን” ተሸጋግራለች ሲሉ ተሳለቁ

    የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባኤ እና አሜሪካ ለድርድር ከምትመርጣቸው የአገሪቱ ባለሥልጣናት መካከል አንዱ የሆኑት ሞሐማድ ባግሄር ጋሊባፍ ኢራን ውስጥ ተመትቶ መውደቁ በተዘገበው የአሜሪካ ተዋጊ ጄት ላይ ተሳለቁ።

    አፈ ጉባኤው በኤክስ ማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ አሜሪካኖች በኢራን ውስጥ የአገዛዝ ለውጥ ከማምጣት ወደ አብራሪዎቻቸውን ወደ መፈለግ መሸጋገራቸውን በምጸት ጽፈዋል።

    “በተከታታይ ኢራንን ለ37 ጊዜ ካሸነፉ በኋላ፣ ይህ ያለ ስትራቴጂ የጀመሩት ጦርነት አሁን ‘ከአገዛዝ ለውጥ’ ወደ ‘እባካችሁ ፓይለቶቻችንን አፋልጉን’ ወደሚል ደረጃ ወርዷል” ብለዋል ጋሊባፍ።

    ከቀናት በፊት ትራምፕ በኢራን ውስጥ የአገዛዝ ለውጥ መካሄዱን አፈ ጉባኤው የሚካተቱበት አዲሱ የኢራን መሪዎች ትውልድ ከቀደሙት “በጣሙን የተለሳለሱ ጽንፈኞች” እና “ምክንያታዊ” ናቸው ብለው ነበር።

    ሞሐማድ ባግሄር ጋሊባፍ በኤክስ ላይ ጨምረውም “የሚደንቅ ነው። ምን ዓይነት ለውጥ ነው። ፍጹም ብልሆች” ሲሉ በአሜሪካኖች ተሳልቀዋል።

    አንዳንድ ያልተረጋገጡ ዘገባዎች እንደሚያመለክቱት የፕሬዝዳንት ትራምፕ አስተዳደር ጋሊባፍን ቀጣይ አጋር እና ቀጣዩ የኢራን መሪ ሊሆኑ ይችላሉ ብሎ ያምናል።

  16. የወደቀውን የአሜሪካ ተዋጊ ጄት አንድ አብራሪ መታደግ መቻሉን ባለሥልጣናት ተናገሩ

    ኢራን ውስጥ የወደቀው የአሜሪካ ተዋጊ ጄት ውስጥ ከነበሩ ሁለት የአየር ኃይል አባላት መካከል አንዱን መታደግ እንደተቻለ የዋሽንግተን ባለሥልጣናት መናገራቸው ተዘገበ።

    በአሜሪካ የቢቢሲ አጋር የሆነው ሲቢኤስ ኒውስ ሁለት ባለሥልጣናትን ጠቅሶ ባወጣው ዘገባ እንዳመለከተው የወደቀው “ኤፍ-15ኢ” ተዋጊ ጄት ሁለት ሰዎችን ይዞ ነበር።

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ በአገሪቱ ማዕከላዊ ክፍል በሚገኝ አካባቢ የአሜሪካ ተዋጊ ጄትን መትቶ መጣሉን አስታውቋል።

    ማኅበራዊ ሚዲያ ላይ የወጣ እና ቢቢሲ ያረጋገጠው አንዲ ቪዲዮ አንድ የአሜሪካ አውሮፕላን በሁለት ሄሊኮፕተሮች ታጅቦ በደቡባዊ ኢራን የፍለጋ እና የመታደግ ዘመቻ ሲያካሂድ ይታያል።

    በደቡባዊ ኢራን የሚገኘው ኮህጊሉዬህ እና ቦየር አህመድ ግዛት አስተዳዳሪ፤ የተመታውን የአሜሪካ ጄት አብራሪ “በሕይወት መያዝ” ቅድሚያ የሚሰጠው ጉዳይ መሆኑን ተናግረዋል።

    “የጠላት ኃይልን መያዝ ወይም መግደል የተሳካላቸው ሰዎች በተለየ ሁኔታ በአስተዳደሩ ጽህፈት ቤት ይመሰገናሉ” ማለታቸውን የኢራን መገናኛ ብዙኃን ዘግቧል።

  17. ኢራን ውስጥ ስለወደቀው ተዋጊ ጄት መታወቅ ያለባቸው ጉዳዮች

    ማኅበራዊ ሚዲያ ላይ የተለጠፈ እና ኢራን ውስጥ የወደቀው የአሜሪካ ተዋጊ አውሮፕላን ስብርባሪ የሚያሳይ ምሥል የተከሰከሰው “ኤፍ-15ኢ ስትራይክ ኢግል” የጦር ጄት እንደሆነ ያመለክታል።

    የዚህ ጄት ዝርያዎች ከአውሮፓውያኑ 1970ዎቹ ጥቅም ላይ ሲውሉ የነበረ ቢሆንም “ኤፍ-15ኢ” ለመጀመሪያ ጊዜ የተዋወቀው በ1988 ነው። የአንዱ ጄት ዋጋ 100 ሚሊዮን ዶላር ገደማ ነው።

    እንዲህ ዓይነቶቹ ተዋጊ ጄቶች የሚሠሩት ከአየር ወደ ምድር እንዲሁም የአየር ለአየር ተልዕኮዎች እንዲወጡ ተደርጎ ነው።

    የአሜሪካው ጄት ኢራን ውስጥ ድሮኖችን እና ክሩዝ ሚሳዔሎችን ለመምታት ለመከላከያ የአጸፋ የአየር ጥቃት ተጉዞ ሊሆን እንደሚችል ይገመታል።

    ጄቱ ከአየር ወደ ምድር ጥቃት በሚፈጽምበት ወቅት ጥቃት ከመፈጸሙ በፊት ዒላማው ላይ ጨረር የማስቀመጥ እንዲሁም በጂፒኤስ የሚመሩ ትክክለኛ ዒላማ መቺ ተተኳሾችን እና ሌሎች ቦንቦችን የመያዝ አቅም አለው።

    የጦር አውሮፕላኑ ሁለት ሰዎችን መያዝ ይችላል። ጄቱን የሚያበርረው ፓይለት ከፊት የሚቀመጥ ሲሆን የመሣሪያ ሥርዓት መኮንኑ ደግሞ የኋለኛው መቀመጫ ላይ ይሆናል።

    የመሣሪያ ሥርዓት መኮንኑ ከፊት ለፊቱ አራት ስክሪኖች ይኖሩታል። ዒላማዎችን የመምረጥ እና ለጥቃት ዒላማው ተገቢ የሆነው መሣሪያ በአግባቡ መዘጋጀቱን የማረጋገጥ ኃላፊነቶችን ይወጣል።

    ተዋጊ ጄቱ ሁለት ሰዎችን የሚጭን መሆኑ የሥስራ ክፍፍል እንዲኖር ያስችላል። በተለይም አብራሪው ከጠላት ለማምለጥ በሚሞክርበት አስጨናቂ የአየር ከባቢ ውስጥ ጠቃሚ ነው።

    የአሜሪካውን ተዋጊ ጄት እንዲወድቅ ያደረገው ትክክለኛ ነገር ምን እንደሆነ በእርግጠኝነት መናገር ያዳግታል።

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ እንደገለጸው መትቶ ጥሎት ከሆነ ጄቱን የመታው ከምድር ወደ አየር የተወነጨ ሚሳዔል የመሆን ዕድሉ ሰፊ ነው።

    “በኢንፍራ ሬድ’ ጨረር የሚመራው የአጭር ርቀት ሚሳዔል ከቦታ ቦታ መንቀሳቀስ ይችላል። በቶሎ ማዘዋወር የሚቻል በመሆኑም ኢራን ውስጥ በሚካሄዱ ዘመቻዎች ላይ ከፍተኛ ስጋትን መደቀኑን ቀጥሏል።

    ጥቃት የተሰነዘረባቸው ተዋጊ ጄቶች የሚቃጠል ጭስ በመልቀቅ ከምድር ላይ የተነሳው ሚሳዔል ዒላማዋን እንዲስት በማድረግ ራሳቸውን ለመከላከል ይሞክራሉ።

    በዚህ ጦርነት ውስጥ የአሜሪካ ወታደራዊ አዛዦች በኢራን የተለያዩ ክፍሎች ላይ የአየር የበላይነት እንዳላቸው ሲናገሩ ነበር።

    ነገር ግን ጄቱ ተመትቶ እንደወደቀ የሚረጋገጥ ከሆነ አሁንም ኢራን ለአሜሪካ የጦር ጄቶች ምን ያህል አደጋ መጋረጥ እንደምትችል ያሳያል።

  18. ዶክተር ቴድሮስ በኢራን ከ20 በላይ የጤና ተቋማት ላይ ጥቃት መፈጸሙን አረጋገጡ

    አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ ጦርነት ከጀመሩበት ጊዜ አንስቶ ከ20 በሚበልጡ የኢራን የሕክምና እና የጤና ተቋማት ላይ ጥቃት መፈጸሙን የዓለም ጤና ድርጅት አረጋገጠ።

    በዚህም በተቋማቱ ላይ ከደረሰው ጉዳት በተጨማሪ አንድ የተላላፊ በሽታዎች ባለሙያ እና ሌላ የኢራን ቀይ ጨረቃ ማኅበር ሠራተኛን ጨምሮ ዘጠኝ ሰዎች ተገድለዋል።

    የድርጅቱ ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ቴድሮስ አድሃኖም በኤክስ ገጻቸው ላይ ባወጡት መግለጫ ከጥቃቶቹ መካከል በቴህራን የሚገኘው ፓስተር ኢኒስቲትዩት እንደሚገኝበት ጠቅሰዋል።

    ኢኒስቲትዩቱ ከአንድ ክፍለ ዘመን በላይ በኢራን የሕብረተሰብ ጤና አገልግሎት ላይ ከፍተኛ ሚና እንደነበረው በመግለጽ ከባድ ጉዳት ስለደረሰበት ከዚህ በኋላ የሕክምና እና የጤና አገልግሎቶችን የማይሰጥበት ደረጃ ላይ እንደሚገኝ ገልጸዋል።

    ዶክተር ቴድሮስ በተለያዩ የኢራን አካባቢዎች ጉዳት የደረሰባቸው የተወሰኑ የጤና አገልግሎት የሚሰጡ፣ የመድኃኒት ማምረቻዎች እና ምርምር የሚካሄድባቸው ተቋማትን በስም በመጥቀስ የደረሰውን ጥቃት አስረድተዋል።

    የእስራኤል ጦር፤ በመድኃኒት ማምረቻው ላይ የተፈጸመውን ጥቃት በተመለከተ በሰጠው ምላሽ ተቋሙ “የኬሚካል ጦር መሳሪያዎችን” ለመሥራት የሚውሉ “ኬሚካሎችን በማስተላለፍ ረገድ ተሳታፊ ነው” ሲል ለጥቃቱ ምንያት አቅርቧል።

  19. ኔትያናሁ የኢራንን 70 በመቶ ገደማ ብረት የምርት አቅምን "አውድመናል" አሉ

    የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔትያናሁ አገራቸው በፈጸመቻቸው ጥቃቶች 70 በመቶ ገደማ የሚሆነው የኢራን ብረታ ብረት የማምረት አቅም መውደሙን ተናገሩ።

    ኔትያናሁ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው በለቀቁት ቪዲዮ፤ በዚህ “ታላቅ ስኬት” የእስላማዊ አብዮታዊ ዘቡን የፋይናንስ እና ወታደራዊ ሀብት ደምስሰናል ብለዋል።

    “በእኔ እና በፕሬዝዳንት ትራምፕ መካከል፣ በእስራኤል መከላከያ ሠራዊት እና በአሜሪካ ሠራዊት መካከል ባለው ሙሉ ትብብር አማካኝነት ኢራንን ማድቀቃችንን እንቀጥላለን" ብለዋል።

    እስራኤል የሊባኖሱን ታጣቂ ቡድ ን"ሄዝቦላህን እግር እግሩን መምታት" እንደምትቀጥልም አክለዋል።

  20. አሜሪካ በኢራን ግዛት ውስጥ ተመትቶ የወደቀ ተዋጊ ጄቷን አብራሪዎችን ለማግኘት ፍለጋ ላይ መሆኗ ተዘገበ

    በኢራን ጥቃት ለመፈጸም ተሰማርቶ የነበረ የአሜሪካ ተዋጊ አውሮፕላን ተመትቶ እንደወደቀ እና አብራሪዎቹን ለማግኘት ጥረት እየተደረገ መሆኑን የኢራን እና የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ።

    ከኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ጋር ግንኙነት ያለው ታስኒም የዜና ወኪል፤ አሜሪካ የኢራን ግዛት ውስጥ ተከስክሷል የተባለውን ተዋጊ ጄት አብራሪዎች እየፈለገች ነው ሲል ዘገበ።

    በተጨማሪ አክሲዮስ፣ ሮይተርስ እ ኒው ዮክ ታይምስ አንድ የአሜሪካን ባለሥልጣናን ጠቅሰው አውሮፕላኑ ተመትቶ መውደቁን እና አብራሪዎቹን ለማግኘት ፍለጋ እየተደረገ መሆኑን ዘግበዋል።

    የአሜሪካ ጦር ማዕከላዊ ዕዝ፤ የአንድ ተዋጊ ጄት ሆርሙዝ ወሽመጥ ውስጥ በሚገኘው ቃሽም ደሴት ተመትቶ ወድቋል የሚለውን የአብዮታዊ ዘቡን መረጃ ሐሙስ ዕለት አስተባብሎ ነበር።

    የማዕከላዊ ዕዙ መግለጫ ያስተባበለው ከሰሞኑ የወጡ የኢራን ዘገባዎችን ስለመሆኑ ግልጽ አይደለም። ቢቢሲ ከዕዙ ተጨማሪ መረጃ ለማግኘት ጠይቋል።

    ታስኒም ዜና ወኪል ባወጣው ዘገባ፤ የአሜሪካ ኃይሎች ከዛሬ ጠዋት ጀምሮ የተዋጊ ጄት አብራሪያዎችን ለማግኘት የፍለጋ ዘመቻ እያከናወኑ ነው ብሏል።

    ዎል ስትሪት ጆርናል በበኩሉ አሜሪካ የተዋጊ ጄቱን አብራሪዎችን ለማግኘት የአሜሪካ ኃይሎች ዘመቻ እያካሄዱ መሆናቸውን ዘግቧል።

    የኢራኑ ታስኒም፤ ፍለጋው የሚከናወነው ሄሊኮፕተሮች፣ አውሮፕላኖች እና የቅኝት ድሮኖችን በመጠቀም እንደሆነም ምንጮችን በመጥቀስ ዘግቧል። የፍለጋ ጥረቱ ግን ፍሬ አላፈራም ብሏል።

    በታስኒም ዘገባ መሠረት፤ የአሜሪካ ተዋጊ ጄት ሲመታ አብራሪዎቹ ከአውሮፕላኑ ወጥተው በኢራን ግዛት ውስጥ አርፈዋል።

    አንድ ኢራን መንግሥት ቴሌቪዥን ጣቢያ በበኩሉ አብራሪዎቹን በሕይወት ለያዘ ሰው ሽልማት አንደሚሰጥ ዘግቧል።

    ቢቢሲ እነዚህን መረጃዎች በገለልተኝነት አላረጋገጠም፤ ተጨማሪ መረጃዎችን ለማሰባሰብ እየሠራ ነው።

    የጦር አውሮፕላኑ ወድቆበታል የተባለው የኢራን ግዛት ባለሥልጣናት አሜሪካዊውያኑን አብራሪዎች ለመያዝ ለነዋሪዎች ጥሪ ያቀረቡ ሲሆን፣ የአካባቢው ነጋዴዎች ደግሞ አብራሪዎቹን ላገኘ ከ50 ሺህ ዶላር በላይ የሚሆን የገንዘብ ሽልማት እንደሚሰጡ አሳውቀዋል።