ባለፈው ምርጫ ብልጽግናን ከወከሉ የአዲስ አበባ ተመራጮች ውስጥ ከ60 በመቶ በላዩ በአዲስ ተተኩ

የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዮስ፣ የብልጽግና ፓርቲ የሕዝብ እና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ዘርፍ ምክትል ኃላፊ ፈዲላ ቢያ፣ ስመጥሩ የሙዚቃ አቀናባሪ ካሙዙ ካሳ እንዲሁም የፍትሕ ሚኒስትር ሃና አርአያስላሴ
የምስሉ መግለጫ, ዘንድሮን ብልጽግና ለአዲስ አበባ ካቀረባቸው አዲስ እጩዎች መካከል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዮስ፣ የብልጽግና ፓርቲ የሕዝብ እና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ዘርፍ ምክትል ኃላፊ ፈዲላ ቢያ፣ ስመጥሩ የሙዚቃ አቀናባሪ ካሙዙ ካሳ እንዲሁም የፍትሕ ሚኒስትር ሃና አርአያስላሴ ይጠቀሳሉ
የንባብ ጊዜ: 4 ደቂቃ

በ2013 ዓ.ም. በተደረገው አጠቃላይ ምርጫ ገዢው ብልጽግና ፓርቲን ወክለው በአዲስ አበባ ከተመረጡት የፓርላማ እና የከተማ ምክር ቤት ተመራጮች ውስጥ 62 በመቶው በአዲስ ተተኩ። በመጪው ምርጫ በአዲስ አበባ ዕጩ ሆነው ካልቀረቡት ተመራጮች መካከል ምክትል ከንቲባው ጃንጥራር አባይ ይገኙበታል።

የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዮስን ጨምሮ በርካታ የፌደራል መንግሥት ከፍተኛ አመራሮች ደግሞ በተወካዮች ምክር ቤት አዲስ አበባን እንዲወክሉ እንዲወዳደሩ በዕጩነት ቀርበዋል።

ብልጽግና ፓርቲ ግንቦት ላይ ይካሄዳል ተብሎ በሚጠበቀው ሰባተኛው አጠቃላይ ምርጫ ለአዲስ አበባ ከተማ ካቀረባቸው 154 ዕጩዎች ውስጥ 96 ያህሉ በባለፈው ምርጫ በመዲናዋ ያልተወዳደሩ እንደሆኑ ቢቢሲ ያደረገው ዳሰሳ ያሳያል።

በስድስተኛው አገር አቀፍ ምርጫ በአዲስ አበባ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እና ለአዲስ አበባ ምክር ቤት ከተመረጡ 160 ግለሰቦች ውስጥ በዚህኛውም ምርጫ ዕጩ ሆነው የቀረቡት 58 ያህሉ ብቻ ናቸው።

ቢቢሲ የተመለከተው የዕጩዎች ዝርዝር እንደሚያመለክተው ገዢው ፓርቲ በአዲስ አበባ ከተማ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንዲወዳደሩ ያቀረባቸው ዕጩዎች 20 ናቸው። ከዚህ ውስጥ በድጋሚ ለዚህ ስፍራ ዕጩ የሆኑት አራቱ ብቻ ናቸው።

ፓርቲው ባለፈው ምርጫ ለፓርላማ ዕጩ ያላቀረበው የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ የማኅበራዊ ጉዳዮች አማካሪ ሚኒስትር የሆኑት ዳንኤል ክብረት በግል በተወዳደሩበት "ምርጫ ክልል 28" ነበር።

በዘንድሮው የዕጩዎች ዝርዝር ውስጥ ዳንኤል ክብረት አልተካተቱም። ብልጽግና ፓርቲም የፌደራል የአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር የሆኑትን ዶ/ር ሌሊሴ ነሜን በምርጫ ክልሉ ዕጩ አድርጎ አቅርቧል።

ፓርቲው ዕጩ ካላስመዘገበባቸው ሦስት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ምርጫ ክልሎች ውስጥ በሁለቱ የሚወዳደሩት የተቃዋሚው የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትሕ (ኢዜማ) አመራሮች ናቸው።

በየካቲት መጨረሻ በተካሄደው የኢዜማ አስቸኳይ ጠቅላላ ጉባኤ የፓርቲው መሪ ሆነው የተመረጡት ኢዮብ መሣፍንት ብልጽግና ዕጩ ባላቀረበበት "ምርጫ ክልል 18" ይወዳደራሉ። በዚሁ ጉባኤ ምክትል መሪ የሆኑት ንጋቱ ወልዴ ደግሞ በ"ምርጫ ክልል 23" የተወካዮች ምክር ቤት ዕጩ ሆነው ቀርበዋል።

ብልጽግና ፓርቲ ዕጩ ባላስመዘገበበት ሌላኛው "ምርጫ ክልል 11" ከሚወዳደሩ ፖለቲከኞች መካከል ደግሞ በስድስተኛው አገር አቀፍ ምርጫ የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄን (አብን) ወክለው ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባልነት የተመረጡት አበባው ደሳለው ይገኙበታል።

በባለፈው ምርጫ በአማራ ክልል የወከሉትን ፓርቲ የለቀቁት አበባው፤ የኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲን (ኢሕአፓ) ተቀላቅለዋል። አሁን ዕጩ ሆነው የቀረቡትም ኢሕአፓ የሚገኝበትን "ትብብር ለኢትዮጵያ አንድነት" የተሰኘ ቅንጅትን በመወከል ነው።

የአዲስ አበባ ምክትል ከንቲባ ጃንጥራር አባይ (ግራ) ዘንድሮ የሚወዳደሩት አማራ ክልል ሲሆን የቀድሞ ከተማዋ ሰላም እና ጸጥታ ቢሮ ኃላፊ ቀነዓ ያደታም በኦሮሚያ ክልል እጩ ሆነዋል። ዶ/ር ሲሳይ መንግሥቴ (መሀል) የእጩዎች ዝርዝር ውስጥ አልተካተቱም
የምስሉ መግለጫ, የአዲስ አበባ ምክትል ከንቲባ ጃንጥራር አባይ (ግራ) ዘንድሮ የሚወዳደሩት አማራ ክልል ሲሆን የቀድሞ ከተማዋ ሰላም እና ጸጥታ ቢሮ ኃላፊ ቀነዓ ያደታም በኦሮሚያ ክልል እጩ ሆነዋል። ዶ/ር ሲሳይ መንግሥቴ (መሀል) የእጩዎች ዝርዝር ውስጥ አልተካተቱም

የትኛዎቹ ተመራጮች በዕጩነት ሳይቀርቡ ቀሩ?

Skip podcast promotion and continue reading
የቢቢሲ አማርኛ ዩቲዩብ ቻናል

ዜና፣ ትንታኔ እና ታሪኮችን በምሥል እና በድምጽ ለማግኘት

ይህንን በመጫን ሰብስክራይብ ያድርጉ

End of podcast promotion

ገዢው ፓርቲ ለአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት እንዲወዳደሩ ካቀረባቸው 134 ዕጩዎች ውስጥ ባለፈው ምርጫም ለዚህ ስፍራ የተወዳደሩት 51 ያህሉ ብቻ ናቸው።

ከንቲባ አዳነች አቤቤ፣ የሰላም እና ፀጥታ ቢሮ ኃላፊ ሊዲያ ግርማ እንዲሁም የጤና ቢሮ ኃላፊው ዶ/ር ዮሐንስ ጫላ በድጋሚ ዕጩ የሆኑት የከተማዋ ከፍተኛ አመራሮች ናቸው።

በአሁኑ የዕጩዎች ዝርዝር ውስጥ ካልተካተቱት ከፍተኛ ባለሥልጣናት አንዱ ከመስከረም 2014 ዓ.ም. አንስቶ የአዲስ አበባ ከተማ ምክትል ከንቲባ ሆነው እያገለገሉ ያሉት ጃንጥራር አባይ ናቸው። ምክትል ከንቲባው በዘንድሮ ምርጫ የሚወዳደሩት በአማራ ክልል ሰሜን ወሎ ዞን "መቄት 1" ለክልሉ ምክር ቤት ነው።

በአዲስ አበባ ምክር ቤት ስብሰባዎች ላይ ሞጋች ጥያቄዎችን በማቅረብ የሚታወቁት የብልጽግና ተመራጩ ዶ/ር ሲሳይ መንግሥቴም የዕጩዎች ዝርዝር ውስጥ የሉም። በተመሳሳይ ጥያቄ አቀራረባቸው የሚጠቀሱት እና ከ2015 ዓ.ም. ጀምሮ በእስር ላይ ያሉት ዶ/ር ካሳ ተሻገርም ተተክተዋል።

ከፍተኛ የመንግሥት አመራር የነበሩት በአሜሪካ የኢትዮጵያ አምባሳደር ዶ/ር ስለሺ በቀለ፣ የጤና ሚኒስትር ዶ/ር ሊያ ካሳ፣ የትራንስፖርት ሚኒስትር ዳግማዊት ሞገስ በዕጩነት ያልቀረቡ የአዲስ አበባ ተመራጮች ናቸው።

በ2016 ዓ.ም. ከሥራ እና ክህሎት ሚኒስትር ዲኤታነት የተነሱት ንጉሡ ጥላሁን፣ ከአገር የሸሹት የቀድሞው ሰላም ሚኒስትር ዲኤታ ዶ/ር ስዩም መስፍን እንዲሁም የቀድሞው የአዲስ አበባ ከተማ ኮሚዩኒኬሽን ኃላፊ ዶ/ር ዮናስ ዘውዴም ከተተኩ የቀድሞ ባለሥልጣናት ውስጥ ተጠቃሽ ናቸው።

አዲስ አበባን ወክለው ፓርላማ ተመራጭ የነበሩት አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ዘንድሮ ዕጩ የሆኑት ለአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት ነው።

በርካታ የፌደራል መንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣናት በአዲስ አበባ ብልጽግናን ወክለው ቀርበዋል
የምስሉ መግለጫ, በርካታ የፌደራል መንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣናት በአዲስ አበባ ብልጽግናን ወክለው ቀርበዋል

አዲሶቹ ዕጩዎች እነ ማን ናቸው?

ብልጽግና ሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አዲስ አበባን እንዲወክሉ ካቀረባቸው 20 ዕጩዎች ውስጥ 16 ያህሉ የፌደራል መንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣናት ናቸው።

የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ጌዲዮን ጢሞቲዮስ፣ የጤና ሚኒስትር ዶ/ር መቅደስ ዳባ እንዲሁም የመንግሥት ኮሚዩኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር እናትአለም መለሰ ተጠቃሽ ናቸው።

በስድተኛው አጠቃላይ ምርጫ የከተማ ምክር ቤት አባል ሆነው የተመረጡት የመስኖ እና ቆላማ አካባቢዎች ሚኒስትር ዶ/ር አብርሃም በላይ እንዲሁም የቱሪዝም ሚኒስትር ሰላማዊት ካሳ አሁን ለተወካዮች ምክር ቤት ታጭተዋል።

የኢትዮጵያ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ወርቁ ጋቸና፣ የጤና ሚኒስትር ዲኤታዋ ሰሃረላ አብዱላሂ፣ የጉምሩክ ኮሚሽነሩ ደበሌ ቃበታ እንዲሁም የኢሚግሬሽን እና ዜግነት አገልግሎት ዋና ዳይሬክተሯ ሰላማዊት ዳዊት ለተወካዮች ምክር ቤት ከቀረቡ ዕጩዎች መካከል ይገኙበታል።

ብልጽግና ፓርቲ ከፍተኛ የፌደራል አመራሮችን ዕጩ ያደረገው ከፓርላማ ብቻ አይደለም። የፍትሕ ሚኒስትሯ ሃና አርአያሥላሴ እና የማዕድን ሚኒስትሩ ሀብታሙ ተገኝ ለከተማዋ ምክር ቤት አባልነት ታጭተዋል። የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት ኃላፊ እና የካቢኔ ጉዳዮች ሚኒስትሯ ዓለምፀሐይ ጳውሎስም ለዚሁ ምክር ቤት ዕጩ ሆነዋል።

የብልጽግና ፓርቲ የሕዝብ እና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ዘርፍ ምክትል ኃላፊ የሆኑት እንዲሁም በማኅበራዊ ሚዲያ ተሳትፏቸው የሚታወቁት ፈዲላ ቢያ በኮልፌ ቀራኒዮ ክፍለ ከተማ ለአዲስ አበባ ምክር ቤት ይወዳደራሉ።

ብልጽግና ፓርቲ የከተማዋ ምክር ቤትን እንዲቀላቀሉ ካቀረባቸው ዕጩዎች መካከል በመዝናኛ ኢንዱስትሪ ተሳትፏቸው የሚታወቁ ግለሰቦችም ይገኙበታል።

ስመጥሩ የሙዚቃ አቀናባሪው ካሙዙ ካሳ በየካ ክፍለ ከተማ በዕጩነት ቀርቧል። የቀድሞው የኢቲቪ መዝናኛ ፕሮግራም አቅራቢ እና ዘንድሮ ለዘጠነኛ ጊዜ የተካሄደው ኦዳ አዋርድ አዘጋጅ በሻቱ ቶለማሪያምም በዚሁ ክፍለ ከተማ ትወዳደራለች።

አርሶ አደር፣ ባለሀብት እና መምህር እንደሆኑ የተገለጹ ዕጩዎችም ብልጽግናን ወክለው ቀርበዋል።