አሜሪካ እና ኢራን አንዳቸው በሌላኛቸው ላይ “ሲኦልን” እንደሚያመጡ ዛቱ

የፎቶው ባለመብት, Reuters
የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ለ10 ቀናት አራዝመውት የነበረው ቀነ ገደብ እየተጠናቀቀ መሆኑን ተከትሎ ኢራን ስምምነት ላይ የማትደርስ ከሆነ አገሪቱ ላይ “ሲኦልን እንደሚያዘንቡ” አስጠነቀቁ።
የኢራን ጦር ከፍተኛ ወታደራዊ አዛዥ የሆኑት ጄነራል አሊ አብዶላሂ አሊአባዲ በበኩላቸው የትራምፕ ንግግር በመጥቀስ “የሲኦል ደጆች ይከፈቱላችኋል” ብለዋል።
አሜሪካ እና ኢራን አንዳቸው ወደሌላኛቸው ዛቻ የሰነዘሩት ሁለቱም የጠፋውን አሜሪካው የአየር ኃይል ባልደረባ እያፈላለጉ ሳለ ነው። አሁን የአብራሪው መገኘቱን ፕሬዝዳንት ትራምፕ አስታውቀዋል።
ፕሬዝዳንት ትራምፕ ከዚህ አስቀድሞ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሑፍ፤ ኢራን “ስምምነት ላይ እንድትደርስ” የሰጡት የተጨማሪ 10 ቀናት ሲጠናቀቅ የአገሪቱ ኃይል ማመንጫዎች ላይ ጥቃት እንደሚፈጽሙ በድጋሚ ዝተዋል።
ኢራን በ48 ሰዓታት ውስጥ ስምምነት ላይ ለመድረስ ካልቻለች ወይም የሆርሙዝ ወሽመጥን ካልከፈተች “ሲኦል ይወርድባቸዋል” ብለዋል።
ትራምፕ የሰጡትን ቀነ ገደብ ውድቅ ያደረገችው ኢራን ግን ዛቻውን አጣጥላለች። የኢራን ማዕከላዊ ዕዝ አዛዥ የሆኑት ጄነራል አሊአባዲ፤ የትራምፕን ዛቻ “የረዳት አልባነት፣ የድንጋጤ፣ ሚዛኑን የሳተ እና የሞኝነት ተግባር" ሲሉ ጠርተውታል።
የኢራን ጦር ማዕከላዊ ዋና መሥሪያ ቤት ኻታም አል አንቢያ ቃል አቀባይ ኢብራሂም ዞልፋጋሪ በበኩላቸው “ጠብ ጫሪነቱ የሚቀጥል ከሆነ መላ ቀጣናው ሲኦል ይሆልናችኋል። የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክን የማሸነፍ ቅዠት፤ የምትሰምጡበት አዘቅት ይሆናል” ሲሉ ዝተዋል።
አሜሪካ እና እስራኤል የኢራንን ወታደራዊ፣ የኤነርጂ እና ሌሎች የኢንዱስትሩ ስፍራዎች መደብደብ ቀጥለዋል።
ኩዌት ደግሞ በኢራን ድሮኖች በተፈጸመ ጥቃት ሁለት ኃይል ማመንጫ ጣቢያዎች እና ውሃን ከጨው ማጣሪያ ስፍራ መመታታቸውን አስታውቃለች።
















