ቀጥታ, በኢራን የሚደገፉት ሁቲዎች ጦርነቱ ከተጀመረ ለመጀመርያ ጊዜ ወደ እስራኤል ሚሳዔል አስወነጨፉ

በመካከለኛው ምሥራቅ እስራኤል እና አሜሪካ ከኢራን ጋር የጀመሩት ጦርነት አንድ ወር ሲሞላው የሁቲ ታጣቂዎች ወደ እስራኤል ሚሳዔል ተኩሰዋል። በኢራን የሚደገፉት የየመን ታጣቂዎች ጦርነቱ ከተጀመረ ለመጀመርያ ጊዜ ነው በእስራኤል ላይ ጥቃት የሰነዘሩት።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. የፓኪስታኑ ጠቅላይ ሚኒስትር ከኢራኑ ፕሬዚዳንት ጋር ተነጋገሩ

    የፓኪስታን ጠቅላይ ሚኒስትር ሼህባዝ ሻሪፍ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የፓኪስታን ጠቅላይ ሚኒስትር ሼህባዝ ሻሪፍ

    የፓኪስታን ጠቅላይ ሚኒስትር ሼህባዝ ሻሪፍ ከኢራኑ ፕሬዚዳንት ማሱድ ፔዜሽኪያን ጋር በስልክ መወያየታቸውን ገለጹ።

    ሁለቱ ባለሥልጣናት ከአንድ ሰዓት በላይ በፈጀው የስልክ ውይይታቸው “ዝርዝር ጉዳዮችን" መወያየታቸውን ገልጸዋል።

    ሻሪፍ በኤክስ ገጻቸው ላይ ከአሜሪካ እና የባህረ ሰላጤው አገራት ጋር "ውይይቶችን በማመቻቸት እና ግጭቶችን በማርገብ" ዙሪያ በማሳተፍ ረገድ “ፓኪስታን እያደረገች ስላለው ቀጣይነት ያለው ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት አሳውቄያቸዋለሁ” ሲሉ አስፍረዋል።

    ፓኪስታን ከዚህ ወደም በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የሚደረግ ንግግርን ለማዘጋጀት ጥያቄ አቅርባ ነበር።

    ሻሪፍ እስራኤል በቴህራን ላይ የምትፈጽመውን ድብደባ አውግዘው ፓኪስታን “ከጀግኖች የኢራን ሕዝቦች ጎን ትቆማለች” ብለዋል።

  2. ሁቲዎች ቀይ ባሕርን የሚያጠቁ ከሆነ ሁኔታው የከፋ ሊሆን ይችላል - የመካከለኛው ምሥራቅ ተንታኝ

    የሁቲ ተዋጊዎች በህዳር 2016 ዓ.ም. በቀይ ባሕር የሚያልፍ መርከብ ላይ ወጥተው

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የሁቲ ተዋጊዎች በህዳር 2016 ዓ.ም. በቀይ ባሕር የሚያልፍ መርከብ ላይ ወጥተው

    በኢራን የሚደገፉት ሁቲዎች ባለፈው አንድ ወር እጃቸውን ሰብስበው የተቀመጡበትን የመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት በዛሬው ዕለት ተቀላቅለዋል። የየመኖቹ ታጣቂዎች ወደ ኢራን ሚሳዔል ማስወንጨፋቸውን ተናግረዋል። የእስራኤል መከላከያ ሠራዊትም ከየመን ሚሳዔል መወንጨፉን ገልጾ ነበር።

    በቻታም ሀውስ የምርምር ባልደረባ የሆኑት ፋሬያ አል ሙስሊም “በሌላኛው ወሳኝ ዓለም አቀፍ የንግድ መስመር” ላይ የተቀመጡት ሁቲዎች በኢራን ጦርነት ውስጥ መሳተፋቸው “ትልቅ ትርጉም” እንዳለው ተናግረዋል።

    ሁቲዎች እስካሁን ቀይ ባሕር ላይ ጥቃት እንደሚፈጽሙ አለመግለጻቸውን ተመራማሪው ‘ቱዴይ’ ለተሰኘው የቢቢሲ የራዲዮ ፕሮግራም አስረድተዋል። ባለሙያው ሁቲዎች “ራሳቸውን ከሌላ የአሜሪካ ጥቃት ለማትረፍ እየሞከሩ” ሊሆን ይችላል የሚል ምልከታ አላቸው።

    የፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር ሁቲዎች በቀጣናው ጥቃት እንዳይፈጽሚ ለማድረግ ከዩናይትድ ኪንግደም ጋር በመሆን በ2025 በቦንብ የመደብደብ ዘመቻ ከፍቶ ነበር።

    ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥን ሙሉ በሙሉ ለመዝጋት እየዛተች ባለችበት በዚህ ጊዜ ሁቲዎች የቀይ ባሕርን ጉዞ የሚያግዱ ከሆነ ምን ሊፈጠር እንደሚችል ለባለሙያው ጥያቄ ቀርቦላቸዋል። አል ሙስሊም “አስፈሪ ነው። አሁንም አስፈሪ ቅዠት ውስጥ ነው ያለነው፤ ይሄ ደግሞ ከቅዠቶች ሁሉ የከፋው ነው” ብለዋል።

    የጋዛ ጦርነት ከተጀመረ በኋላ ሁቲዎች በቀይ ባሕር የሚያልፉ መርከቦችን ሲያጠቁ እና ወደ እስራኤል ሚሳዔል ሲተኩሱ ነበር። ይህንን እርምጃ የወሰዱትም ለፍልስጤማውያን ያላቸውን አጋርነት ለማሳየት እንደሆነ በወቅቱ ገልጸዋል።

    ሁቲዎች በባሕር መስመሩ የሚያልፉ የንግድ መርከቦችን በድሮን እና በሚሳዔል ሲያጠቁ ነበር። ጀልባዎች እና ሄሊኮፕተር በመጠቀምም በቀይ ባሕር መጓዝን አስቸጋሪ አድርገውት ነበር።

    በዚህም ምክንያት ኩባንያዎች የመርከቦቻቸውን የቀይ ባሕር መስመር በመቀየር በሌላ አቅጣጫ ረጅም ጉዞ ለማድረግ ተገድደዋል።

  3. ሳዑዲ አረቢያ፣ ቱርክ እና ግብፅ በቀጣናው ያለውን ግጭት ለማርገብ በፓኪስታን ሊወያዩ ነው

    የፓኪስታን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኢሻቅ ዳር

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የፓኪስታን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኢሻቅ ዳር

    የፓኪስታን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኢሻቅ ዳር አገራቸው የሳዑዲ አረቢያ፣ የቱርክ እና የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮችን እአአ ከመጋቢት 29-30 በዋና ከተማዋ ኢስላማባድ እንደምታስተናግድ ገለፁ።

    ሚኒስትሮቹ “ቀጣናው ውስጥ ያለውን ውጥረት ለማርገብ በሚደረጉ ጥረቶች ላይ” አተኩረው እንደሚወያዩ ዳር በኤክስ ገጻቸው ጽፈዋል።

    የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ውይይቱ በፓኪስታን ዋና ከተማ እንደሚካሄድ እና ለዚህም ሚኒስትሩ ወደ ስፍራው ማምራታቸውን የሚያረጋግጥ መግለጫ አውጥቷል።

    ፓኪስታን በቀጣናው የሰላም አደራዳሪነት ሚና ለመጫወት ጥረት እያደረገች ነው።

    ኢስላማባድ በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የሚደረገውን ውይይት ለማስተናገድ ሀሳብ አቅርባለች። እነዚህ ውይይቶች ይካሄዱ እንደሆነ እስካሁን ምንም ዓይነት ማረጋገጫ አልተገኘም።

    በዚህ ሳምንት መጀመሪያ ላይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ"በፓኪስታን በኩል በሚተላለፉ መልዕክቶች" አማካኝነት ሁለቱ አገራት "ቀጥተኛ ባልሆነ መንገድ ውይይቶች እያደረጉ" መሆኑን ገልጸው ነበር።

    ትራምፕ በዚህ ሳምንት መጀመሪያ ላይ የፓኪስታን ጠቅላይ ሚኒስትር ሼህባዝ ሻሪፍ የጻፉትን የኤክስ ልጥፍ ፎቶ በማንሳት በትሩዝ ሶሻል ገጻቸው ላይ አጋርተዋል።

    ሻሪፍ በጻፉት ጽሑፍ ፓኪስታን የሚደረጉ ንግግሮችን ለማስተናገድ "ዝግጁ" እንደሆነች ተናግረዋል።

  4. ሩሲያ በዩክሬን የተጠቀመችውን የድሮን ቴክኖሎጂ በማሻሻል ለኢራን እያቀረበች መሆኑ ተዘገበ

    ኢራን በዩክሬን ጦርነት ወቅት ለሩሲያ ድሮን ስታቀርብ ነበር

    የፎቶው ባለመብት, Iranian Army/Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ኢራን በዩክሬን ጦርነት ወቅት ለሩሲያ ድሮን ስታቀርብ ነበር

    ሩሲያ፤ የተለያዩ አይነት ድሮኖችን ለኢራን እያቀረበች መሆኑን ከአሜሪካ እና ከአውሮፓ ባለሥልጣናት መስማቱን አሶሺዬትድ ፕሬስ ዜና ወኪል ዘገበ። ከተላኩት መሣሪያዎች መካከል ሩሲያ ዩክሬንን ከወረረች በኋላ ከኢራን የቀረበላትን የድሮን ቴክኖሎጂ የተሻሻለ ስሪት እንደሚገኝበትም ተገልጿል።

    ጦርነት የተከፈተባት ኢራን ላለፈው አንድ ወር ወደ እስራኤል፣ የባህረ ሰላጤው ጎረቤቶቿ እና በመካከለኛው ምሥራቅ የሚገኙ አሜሪካ የጦር ሰፈሮች ድሮኖችን በመላክ ጥቃት ስትፈጽም ቆይታለች። ኢራን በራሷ የሻሄድ ድሮን ክምችት አላት።

    ሩሲያ በበኩሏ ከዚህ ቀደም ቴህራን ያገኘቻቸውን የመጓዝ አቅማቸውን ጭምር በመጨመር የድሮኖቹን ዲዛይን ማሻሻሏን የኤፒ ዘገባ ያመለክታል።

    የሩሲያ እና ኢራን ባለሥልጣናት ድሮኖች ከሞስኮ ወደ ቴህራን የሚተላለፉበትን መንገድ በተመለከተ ውይይት ማድረጋቸውን አንድ አውሮፓ የስላላ ኃላፊ ለዜና ወኪሉ ተናግረዋል። የአሜሪካ የመከላከያ ባለሥልጣን በበኩላቸው፤ ይህ ድሮን የማጓጓዝ ዕቅድ የአንድ ጊዜ ይሁን በተከታታይ የሚደረግ ግልጽ አለመሆኑን ተናግረዋል ተብሏል።

    ዘገባው እንደሚያስረዳው ሁለቱም ባለሥልጣናት ምን ያህል ድሮኖች እንደሚላኩ ወይም ምን ያህል ወሳኝ እንደሆነ አልገለጹም። ሌላ የአውሮፓ ባለሥልጣን በበኩላቸው ብዛቱ አነስተኛ የሆነ ድሮን በጦርነቱ ውስጥ የሚኖረው ውጤት አነስተኛ እንደሚሆን ጠቁመዋል።

  5. የኩዌት ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ በድሮን ተመታ

    የኩዌት የአየር ማረፊያ በድሮን ተመታ

    የፎቶው ባለመብት, kuna

    የኩዌት ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ በበርካታ ድሮኖች ጥቃት እንደተፈጸመበት የአገሪቱ የሲቪል አቪዬሽን ባለሥልጣን ቃል አቀባይ ለኩዌት የዜና ወኪል ተናገሩ።

    በአየር ማረፊያው ላይ ደረሰው ጉዳት ውስን እንደሆነ እና በሰው ላይ የደረሰ ጉዳት አለመኖሩን መናገራቸውንም ተገልጿል። ጉዳቱ የደረሰው በአየር ማረፊያው የራዳር ስርዓት ላይ እንደሆነ ሮይተርስ የዜና ወኪሉን ጠቅሶ ዘግቧል።

    የኩዌት ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ጥቃት ሲፈጸምበት ይህ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። ረቡዕ ዕለት በኢራን ድሮን በተፈጸመ ጥቃት የአገሪቱን የነዳጅ ማጠራቀሚያ ዒላማ ተደርጎ ነበር።

  6. በሊባኖስ የተፈጸመን ጥቃት የሚያሳይ ምስል

    የሊባኖስ መንግሥታዊ የዜና ወኪል እስራኤል በደቡባዊ የአገሪቱ ክፍል በሚገኙ በርካታ ከተሞች ላይ ተከታታይ ጥቃት ማድረሷን ዘግቧል።

    በሊባኖስ የሚንቀሳቀሰው እና በኢራን የሚደገፈው የሄዝቦላህ ቡድን፣ በሰሜናዊ እስራኤል የሚገኙ የቴል አቪቭ ወታደራዊ ስፍራዎችን ዒላማ ያደረገ ጥቃት መፈጸሙን ገልጿል።

    የሕይወት አድን ሠራተኞች በደቡባዊ ሊባኖስ ሳክሳኪያህ ከተማ በሚገኝ ሕንፃ ላይ ያነጣጠረ የእስራኤል የአየር ጥቃት ያደረሰውን ጉዳት ሲመለከቱ

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የሕይወት አድን ሠራተኞች በደቡባዊ ሊባኖስ ሳክሳኪያህ ከተማ በሚገኝ ሕንፃ ላይ ያነጣጠረ የእስራኤል የአየር ጥቃት ያደረሰውን ጉዳት ሲመለከቱ
    የእስራኤል መከላከያ አባላት በሊባኖስ ነዋሪዎች ናባቲህን ለቅቀው እንዲወጡ ቢያስጠነቅቁም ላልወጡ ሰዎች ምግብ ሲያከፋፍሉ

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የእስራኤል መከላከያ አባላት በሊባኖስ ነዋሪዎች ናባቲህን ለቅቀው እንዲወጡ ቢያስጠነቅቁም ላልወጡ ሰዎች ምግብ ሲያከፋፍሉ
    በቤይሩት ደቡባዊ ክፍል የእስራኤል አየር ድብደባ ያደረሰውን ውድመት ተከትሎ ፍርስራሽ የሚያፀዳ ቡልዶዘር

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, በቤይሩት ደቡባዊ ክፍል የእስራኤል አየር ድብደባ ያደረሰውን ውድመት ተከትሎ ፍርስራሽ የሚያፀዳ ቡልዶዘር
    የእስራኤል ጦር በደቡባዊ ሊባኖስ ወደሚገኙ አካባቢዎች ሲሰማራ

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የእስራኤል ጦር በደቡባዊ ሊባኖስ ወደሚገኙ አካባቢዎች ሲሰማራ
  7. ሌሊቱን በባሕረ ሰላጤው አገራት እና ኢራን ላይ የተፈጸሙ ጥቃቶች

    በኢራን ዋና ከተማ ቴህራን የሚሳዔል ጥቃቶች ሌሊቱን መቀጠላቸው ተሰምቷል። ኢራን በበኩሏ ወደ እስራኤል እና የባሕረ ሰላጤው አገራት ሚሳዔሎች መተኮሷ ተገልጿል።

    • የእስራኤል አምቡላንስ አገልግሎት አርብ ዕለት ኢራን ያስወነጨፈችው ሚሳዔል በማዕከላዊ እስራኤል በርካቶች ላይ ጉዳት ማድረሱን እና አንድ የ52 ዓመት ሰው መሞታቸውን አስታውቋል።
    • የእስራኤል ጦር በበኩሉ ከየመን የተወነጨፈ ሚሳዔልን ማክሸፉን ገልጿል።
    • በደቡባዊ ኦማን በሳላህ ወደብ ላይ በተፈጸመ ሁለት የድሮን ጥቃት አንድ የውጭ አገር ዜጋ መጎዳቱን የአገሪቱ ባለሥልጣናት ተናግረዋል።
    • በዩኤኢ፣ ኩዌት እና ባሕሬን እንዲሁ የአየር መቃወሚያዎች የሚተኮሱ ድሮኖችን ማክሸፋቸው ተገልጿል። በዩኤኢ አቡዳቢ የሚሳዔል ስብርባሪ አምስት ሰዎች ላይ ጉዳት አድርሷል።
    • የሳዑዲ አረቢያ መከላከያ ሚኒስቴር ወደ ሪያድ የተተኮሱ ሦስት ድሮኖችን እና ባለስቲክ ሚሳዔል ማክሸፉን አስታውቋል። አርብ ዕለት በልዑል የአየር ኃይል ላይ በደረሰ ጥቃት 12 የአሜሪካ ወታደሮች መጎዳታቸው ተሰምቷል።
  8. እስራኤል ከየመን ሚሳዔል እንደተተኮሰባት ገለጸች

    የየመን ሁቲዎች ኢራንን በመደገፍ ጦርነቱን እንደሚቀላቀሉ አስታውቀው ነበር

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የየመን ሁቲዎች ኢራንን በመደገፍ ጦርነቱን እንደሚቀላቀሉ አስታውቀው ነበር

    የእስራኤል መከላከያ ሠራዊት ከየመን ሚሳዔል መተኮሱን እንደለየ አስታወቀ። የዜና ወኪሎቹ ሮይተርስ እና አጃንስ ፍራስ ፕሬስ (ኤኤፍፒ)፤ አንድ ወር የሞላው የኢራን ጦርነት ከተጀመረ ወዲህ ከየመን ወደ እስራኤል ሲተኮስ ይህ የመጀመሪያው እንደሆነ ዘግበዋል።

    የእስራኤል ጦር በቴሌግራም ገጹ ባሰፈረው መልዕክት፤ መከላከያ ሠራዊቱ ከየመን ወደ እስራኤል ግዛት ሚሳዔል መተኮሱን ለይቷል፤ የአየር መከላከያ ስርዓቶች ስጋቱን ለመቀልበስ እየሰሩ ነው” ብሏል። ከ15 ደቂቃ ካነሰ ቆይታ በኋላም በመላ አገሪቱ የሚገኘው ሕዝብ ጥብቅ ከሆኑትን ስፍራዎች መውጣት እንደሚችሉ አስታውቋል።

    እስራኤል ሚሳዔል እንደተተኮሰባት የገለጸችው በኢራን የሚደገፈው የየመኑ ሁቲ ቃል አቀባይ ቴህራን ላይ የሚፈጸመው ጥቃት የሚቀጥል ከሆነ አማጺው ቡድን የመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነትን እንደሚቀላቀል ከተናገሩ በኋላ ነው።

    የመኑ ጦር ኃይሎች የተባለው የሁቲ ወታደራዊ ክንፍ ቃል አቀባይ የሆኑት ያህያ ሳሪ ቴሌግራም ላይ ባወጡት መግለጫ፤ ሦስት ሁኔታዎች የሚፈጸሙ ከሆነ “ወታደራዊ ጣልቃ ገብነት ለማድረግ ጣቶቻችን ቃታው ላይ ናቸው” ብለዋል።

    ቃል አቀባዩ የገለጿቸው ሦስት ሁኔታዎች የሚከተሉት ናቸው፦

    • አሜሪካ እና እስራኤል ኢራን ላይ የከፈቱትን ጦርነት ሌላ አገር የሚቀላቀል ከሆነ
    • አሜሪካ እና እስራኤል “ቀይ ባሕርን በኢራን እስላማዊ ሲፐብሊክ እና ማንኛውም ሙስሊም አገር ለሚፈጸመው ጠበኛ ዘመቻ የሚጠቀሙ ከሆነ”
    • ኢራን ላይ የሚካሄደው “ግጭት የሚባባስ” ከሆነ

    መግለጫው አክሎም፤ ይህ እርምጃ "ጠላቶቹ አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ፣ በፍልስጤም እና ጋዛ፣ በኢራቅ እንዲሁም በሊባኖስ ላይ ለሚፈጽሙት የቀጠለ ጥቃት" የተሰጠ ምላሽ መሆኑን ገልጿል።

  9. አንድ ወር በሞላው የኢራን ጦርነት ምን ያህል ሰላማዊ ሰዎች ተገደሉ?

    በኢራን በተፈጸመ ጥቃት የፈረሰ የመኖርያ ሕንጻ

    የፎቶው ባለመብት, Shutterstock

    የምስሉ መግለጫ, በኢራን በተፈጸመ ጥቃት የፈረሰ የመኖርያ ሕንጻ

    መቀመጫውን አሜሪካ ያደረገው የሰብዓዊ መብቶች አክቲቪስቶች ዜና ወኪል ሃራና፣ አንድ ወሩን ዛሬ በያዘው የኢራን ጦርነት 217 ሕጻናትን ጨምሮ 1464 ሰላማዊ ሰዎች መገደላቸውን ዘግቧል።

    አሜሪካ እና እስራኤል በቴህራን ላይ ጦርነት የከፈቱት የካቲት 21 2018 ዓ.ም. ነበር።

    የእስራኤል መከላከያ ከ12ሺህ በላይ ቦምቦችን በመላ ኢራን መጠቀሙን ሲገልጽ በቴህራን ብቻ 3,600 ተጠቅሞ ድብደባ ፈጽሟል።

    አሜሪካ እንዲሁ በመላ ኢራን ከ9ሺህ በላይ ዒላማዎችን በመለየት ድብደባ መፈጸሟን ገልጻለች።

    አሜሪካ እና እስራኤል ዒላማ አድርገው ድብደባ የፈጸሙባቸው አብዛኛዎቹ ፖሊስ ጣቢያዎች፣ ወታደራዊ እና ፖሊስ ዩኒቨርስቲዎች፣ የፖሊስ ዋና መሥሪያ ቤት፣ የመጠለያ ቤቶች፣ የአብዮታዊ ዘብ ቤቶች፣ እንዲሁም ኬላዎች እና የጦር መሣሪያ ማከማቻዎች ይሆናሉ ተብለው የሚታሰቡ ስፈራዎች እንደሆኑ ዘገባው ያስረዳል።

    እነዚህ ዒላማዎች ብዙ ጊዜ የሚገኙት ሰላማዊ ሰዎች በሚኖሩባቸው እና እንቅስቃሴዎች በሚበዛባቸው አካባቢዎች ነው።

    በኢራን ጥቃት ሲፈጸም የተመለከተ ነዋሪ ለቢቢሲ እንደተናገረው በሰላማዊ ሰዎች መኖሪያ የሚፈጸሙ ድብደባዎች የመንግሥት ተቃዋሚ የነበሩትን ሁሉ ያስቆጣ ነው።

    ቢቢሲ በሪፖርቱ ላይ ስለተገለጹት የሰላማዊ ሰዎች መኖሪያዎች ለእስራኤል ጦር ጥያቄ ቢያቀርብም ጥቃቶቹ መፈጸማቸውን ከማረጋገጥ ውጪ ተጨማሪ ምላሽ ሳይገኝ ቀርቷል።

    የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስቴር ለጥያቄዎቹ ምላሽ አልሰጠም።

    ኢራን በጦርነቱ ውስጥ የአሜሪካ አጋር በሆኑት የባሕረ ሰላጤው አገራት የሚገኙ አውሮፕላን ማረፊያዎችን፣ ሆቴሎችን እንዲሁም የሰላማዊ ዜጎች መኖሪያዎችን እና ሌሎች መሠረተ ልማቶችን አጥቅታለች።

    በኢራን የኢንተርኔት እና የኮሚኒኬሽን አገልግሎት በተቋረጠበት ሁኔታ በርካቶች ቀጣዩ የጥቃት ዒላማ የቱ እንደሚሆን ለማወቅ እንደማይችሉ በመግለጽ ፍርሃታቸውን ያስረዳሉ።

  10. በሳዑዲ አረቢያ የጦር አውሮፕላን ማረፊያ ላይ በተፈጸመ ጥቃት ቢያንስ 12 የአሜሪካ ወታደሮች ተጎዱ

    ኢራን በሳዑዲ አረቢያ ልዑል ሱልጣን የጦር አውሮፕላን ማረፊያ ላይ በፈጸመችው ጥቃት ቢያንስ 12 የአሜሪካ ወታደሮች ላይ ጉዳት መድረሱን በአሜሪካ የቢቢሲ አጋር የሆነው ሲቢኤስ ዘገበ።

    ጥቃቱ ሲፈጸም በሕንጻው ውስጥ ነበሩ የተባሉ ቢያንስ ሁለት ወታደሮች “በጣም ከባድ ጉዳት” እንደ ደረሰባቸው ዎል ስትሪት ጆርናል ዘግቧል።

    ጥቃቱ የተፈጸመው በአንድ ሚሳዔል እና በበርካታ ድሮኖች ሲሆን በርካታ አየር ላይ ነዳጅ የሚሞሉ አውሮፕላኖችም ጉዳት ደርሶባቸዋል ሲሉ ኒው ዮርክ ታይምስ እና ዎል ስትሪት ጆርናል ዘግበዋል።

    ፔንታጎን እና የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ መገናኛ ብዙኃን ላቀረቡላቸው ጥያቄዎች እስካሁን ድረስ ምላሽ አልሰጡም።

  11. ቴህራን ውስጥ በመኖሪያ ሕንጻ ላይ ጥቃት ተፈጸመ

    ጥቃት የደረሰበት ሕንጻ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ዛሬ አርብ በኢራን ዋና ከተ ማቴህራን ውስጥ በሚገኝ የመኖሪያ ሕንጻ ላይ የተፈጸመ ጥቃትን የሚያሳዩ ፎቶግራፎች እየወጡ ነው።

    ከጥቃቱ በኋላ የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች በፍርስራሾች ውስጥ የተቀበሩ ሰዎችን ለማውጣት ከስፍራው ደርሰው ጥረት ሲያደርጉ ታይተዋል።

    በኢራን ውስጥ ባለው የኢንተርኔት መቋረጥ ምክንያት ፎቶዎችን እና ዝርዝር መረጃዎችን ለማግኘት አዳጋች ሆኗል።

    በተጨማሪም ዓለም አቀፍ የዜና ድርጅቶች ወደ አገሪቱ ገብተው ለመዘገብ የሚያስፈልጋቸውን ቪዛ እና ፈቃድ ማግኘት ስለማይችሉ ከኢራን ዜና እና መረጃ ማግኘት አዳጋች ነው።

    ጥቃት በተፈጸመበት ቦታ የተገኙ ነዋሪዎች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች በጥተቱ ስፍራ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    በፍርስራሽ አካባቢ የሚታዩ ሰዎች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

  12. የዓለም የነዳጅ ዋጋ በማን ነው የሚወሰነው?

    ነዳጅ ማምረቻ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ነዳጅ በዓለም ምጣኔ ሀብት ላይ ከፍተኛ የሆነ ተጽእኖ አለው። የነዳጅ ዋጋ ሲቀንስ የምርቶች ዋጋ እንዲቀንስ እና የአገራት ምጣኔ ሀብት እንዲነቃቃል የማድረጉን ያህል፣ ዋጋው ሲጨምር ደግሞ በሁሉም ዘርፎች ላይ መናጋትን ያስከትላል።

    አሁን እንዳጋጠመው ዓይነት በነዳጅ ምርት እና አቅርቦት ላይ የሚታይ መስተጓጎል የነዳጅ ዋጋ መጨመርን በማስከተል በዓለም ዙሪያ ቀውስን ያስከትላል። ለመሆኑ የነዳጅ ዋጋን ማን ነው የሚወስነው?

    የነዳጅ ዋጋ የሚወሰነው “በገበያ” ነው። በገበያ ሲባል ደግሞ ነዳጅ የሚያመርቱ አገራት እና ኩባንያዎች እንዲሁም የነዳጅ ነጋዴዎች ይገኙበታል።

    አገራት የሚባሉት ነዳጅ አምራች የሆኑ 23 አገራት የነዳጅ ዋጋን ለመቆጣጠር እና ለመወሰን ለገበያ የሚያቀርቡትን ምርት በጋራ ለመወሰን የመሠረቱት ድርጅት ኦፔክ ከፍተኛ ተጽእኖ አለው።

    አገራቱ የነዳጅ ዋጋ በዓለም ገበያ ላይ ዋጋው እንዲጨምር ሲፈልጉ ምርታቸውን ይቀንሳሉ። ዋጋው እንዲወርድ ከስምምነት ሲደርሱ ደግሞ ለገበያ የሚያቀርቡትን ምርት ይጨምራሉ።

    በአሜሪካ መረጃ መሠረት በ2022 የኦፔክ አባል አገራት 59 በመቶውን የዓለም የነዳጅ ፍላጎት ያቀርባሉ። ነገር ግን የነዳጅ ዋጋን ሙሉ ለሙሉ አይቆጣጠሩም።

    በተጨማሪም ሼልን የመሳሰሉ ግዙፍ የነዳጅ ኩባንያዎች እና አሜሪካንን የመሳሰሉ ከኦፔክ ውጪ ያሉ ታላላቅ ነዳጅ አምራቾችም በዋጋው ላይ የራሳቸው ተጽእኖ አላቸው።

    በዋጋው ላይ ሚና ያላቸው ሌሎቹ ደግሞ ግለሰቦች እና የኢንቨስትመን ኩባንዎች ወይም ነዳጅ ገዝተው በገበያ ላይ የሚሸጡ አካላት የሚገኙበት የነዳጅ ነጋዴዎች ናቸው።

    እነዚህ ነጋዴዎች ለወደፊት በሚል ስምምነት በተደረሰበት ዋጋ እና ኮንትራ መሠረት አስቀድመው ከአምራቾች ላይ ነዳጅ ለመግዛት ይስማማሉ። በሌላ አባባል በተንበያ ላይ በመመሥረት ዋጋ ተምነው ነዳጅ ለመግዛት ከጊዜው በፊት ይወስናሉ።

  13. በኢራን ወሳኙ ሥልጣን ያላቸው እነማን ናቸው? የትኞቹስ ተገደሉ?

    ባለፈው አንድ ወር በርካታ የኢራን ከፍተኛ ወታደራዊ እና ፖለቲካዊ መሪዎች በአሜሪካ እና በእስራኤል በፈጸሙባቸው ጥቃቶች ተገድለዋል።

    ነገር ግን ፕሬዝዳንት ትራምፕ እንዳዘዙት ኢራን እጇን ሳትሰጥ ከአሜሪካ ጋር ለመደራደር የራሷን ቅድመ ሁኔታ አቅርባለች።

    አገሪቱን አርባ ዓመታት ለሚጠጋ ጊዜ በበላይነት ያስተዳደሩት ጠቅላይ መሪው አያቶላህ አሊ ኻሜኒን ጨምሮ ቁልፍ መሪዎቿ የተገደሉባት ኢራን ተተኪዎችን በመሰየም ቀጥላለች።

    በኢራን ሥርዓት ውስጥ ወሳኙ ሥልጣን ያላቸው እነማን ናቸው? የትኞቹስ ባለፈው አንድ ወር ውስጥ ተገደሉ? ተጨማሪ እዚህ ያንብቡ አሜሪካ እና እስራኤል ብዙዎቹን የኢራን መሪዎችን ገድለዋል፤ ትራምፕ ከማን ጋር ሊደራደሩ ይችላሉ?

    ፎቶግራፎች
  14. የተባበሩት መንግሥታት በኢራን ትምህርት ቤት ላይ የተፈጸመው ጥቃት እንዲመረምር ጠየቀ

    ከፍርስራሽ ውስጥ ሰዎችን ለማውጣት የሚሞክሩ ሰዎች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ጥቃቱ የተፈጸመበት ሚናብ ውስጥ የሚገኘው ትምህርት ቤት

    የተባበሩት መንግሥታት የሰብአዊ መብቶች ከፍተኛ ኮሚሽነር ቮልከር ተርክ በኢራን ላይ ጥቃት በተከፈተበት በመጀመሪያው ዕለት በደቡብ ኢራን በሴቶች ትምህር ቤት ላይ የተፈጸመው ጥቃት ላይ አስቸኳይ ምርመራ እንዲደረግ ጠየቁ።

    በትምህርት ቤቱ ላይ በተፈጸመው ጥቃት አብዛኞቹ ልጆች የሆኑ 168 ሰዎች መገደላቸውን ባለሥልጣናት የገለጹ ሲሆን፣ የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን መርማሪዎች የአሜሪካ ኃይሎች “ባላሰቡት ሁኔታ” ትምህርት ቤቱን ዒላማ አድርገዋል ብለው እንደሚያምኑ ዘግበዋል።

    የመንግሥታቱ ድርጅት ባለሥልጣን ቮልከር ተርክ በጦርነት ውስጥ ልጆችን በመጠበቅ ዙሪያ በተደረገ ስብሰባ ላይ በትምህርት ቤቱ ላይ “ጥቃቱን የፈጸሙት አስቸኳይ፣ ገለልኛ፣ ግልጽ እና ተጠያቂነት የሚያሰፍን ምርመራ” እንዲየደርጉ ጠይቀዋል።

    ባለሥልጣኑ ጥቃቱ “ከባድ የሆነ አስፈሪ ሁኔታን የፈጠረ በመሆኑ” ምርመራው በአስቸኳይ ተደርጎ ውጤቱም ይፋ እንዲደረግ ባሳሰቡበት ንግግር “ከፍተኛ የአሜሪካ ባለሥልጣናት ጥቃቱ ላይ ምርመራ እየተደረገ መሆኑን” እንደተናገሩ ገልጸዋል።

    ተርክ ጨምረውም "በአገራት መካከል የቱንም ዓይነት ልዩነት ቢኖርም፣ እነዚህ ልዩነቶች ተማሪ ልጆችን በመግደል እንደማይፈቱ ሁላችንም እንስማማለን” ብለዋል፥

    የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት እና አሜሪካ በትምህርት ቤቱ ላይ በተፈጸመው ጥቃት ዙሪያ ምርመራ እያደረጉ መሆናቸውን በተናጠል አሳውቀዋል።

  15. ኢራን በሆርሙዝ በኩል ሊያልፉ የነበሩ ሦስት መርከቦችን መመለሷን አሳወቀች

    በሆርሙዝ በኩል የሚያልፍ በኩል

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ዛሬ ጠዋት በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ሊያልፉ የነበሩ ሦስት የጭነት መርከቦችን ማስመለሱን አስታወቀ።

    "የተለያዩ አገራት ንብረት የሆኑ ኮንቴይነር የጫኑ ሦስት መርከቦች፤ እንዲያልፉ የተፈቀደላቸው መርከቦች በሚጓዙበት የተለየ መስመር በኩል ለማለፍ ሞክረው ነበር። የአብዮታዊ ዘቡ ባሕር ኃይል ማስጠንቀቂያ ከሰጣቸው በኋላ ወደ መጡበት ተመልሰዋል” ይላል የወጣው መግለጫ።

    የአብዮታዊ ዘቡ መግለጫ ጨምሮም "የሆርሙዝ ወሽመጥ የተዘጋ በመሆኑ የትኛውም ለማለፍ የሚሞክር መርከብ ጠንካራ ምላሽ ይጠብቀዋል” ብሏል።

    “የአሜሪካ እና የእስራኤል አጋሮች እና ደጋፊዎች ከሆኑ አገራት ወደቦች የሚነሱ እና ወደዚያ የሚያመራ የትኛውም ዓይነት መርከብ በሆርሙዝ በኩል እንዳያልፍ ተከልክሏል” ብሏል መግለጫው።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ ለአገሪቱ ቴሌቪዥን “ከቻይና፣ ከሩሲያ፣ ከፓኪስታን፣ ከኢራቅ እና ከሕንድ” መርከቦቻቸው በሆርሙዝ በኩል እንዲያልፉ ጥያቄ እንደቀረበላቸው ተናግረዋል።

    ጨምረውም በኢራን ዕይታ ሆርሙዝ “ሙሉ ለሙሉ አልተዘጋም ነገር ግን ለጠላቶቻችን ዝግ ነው” ብለዋል።

  16. ኢራን በመካከለኛው ምሥራቅ ከአሜሪካ ጦር አቅራቢያ ያሉ ነዋሪዎች አካባቢዎቹን ለቅቀው እንዲወጡ አስጠነቀቀች

    የኢራን ጥቃት

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ በመካከለኛው ምሥራቅ አካባቢ የአሜሪካ ጦር ባለባቸው ቦታዎች የሚኖሩ ሰዎች አካባቢውን ለቅቀው እንዲወጡ አስጠነቀቀ።

    ከአብዮታዊ ዘቡ ጋር ግንኙነት ያለው የፋርስ የዜና ወኪል የወጣው የወታደራዊ ኃይሉ መግለጫ፤ አሜሪካ እና እስራኤል "የሲቪል ቦታዎችን እና ንፁኃን ሰዎችን እንደ ሰብአዊ ጋሻ ተጠቅመዋል" ሲል ከስሷል። መግለጫው በተጨማሪ አሜሪካ ሲቪሎችን እና የኢራን ባለሥልጣናትን ገድላለች በማለት ክስ አቅርቧል።

    ጦርነቱ ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ አብዮታዊ ዘቡ በርካታ ማስጠንቀቂያዎችን ሰጥቷል። ከዚህ ቀደም በመካከለኛው ምሥራቅ በአሜሪካ የኢንዱስትሪ ቦታዎች አቅራቢያ የሚኖሩ ነዋሪዎች ለቅቀው እንዲወጡ አስጠንቅቆ ነበር።

    አሁን ባወጣው ማስጠንቀቂያው ላይ ግን ምንም ዓይነት ቦታዎችን በግለጽ ሳይጠቅስ አጠቃላይ ማስጠንቀቂያ ሰጥቷል።

    አንድ ወር በሞላው ጦርነት አብዮታዊ ዘቡ ከፍተኛ አዛዦቹ ተገድለውበታል።

    ምንም እንኳን ኢራን ከቅርብ ቀናት ወዲህ የሟቾችን ቁጥር በይፋ ባታሳውቅም በአሜሪካ የሚገኘው የሰብአዊ መብት ተሟጋች የዜና ወኪል (ህራና) እንደዘገበው፤ እስካሁን 1,492 ሕጻናትን ጨምሮ 221 ኢራናውያን ሲቪሎች ተገድለዋል። 1,167 የኢራን ጦር ሠራዊት አባላት መገደላቸውንም የዜና ወኪሉ ዘግቧል።

  17. እስራኤል የኢራንን ‘ዋነኛ’ የሚሳዔል እና የባሕር ላይ ፈንጂዎች ማምረቻን መምታቷን አስታወቀች

    ሆርሙዝ ወሽመጥ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ተመታ የተባለው ተቋም በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ ስጋት የፈጠሩ የባሕር ላይ ፈንጂዎችን የሚያመርት ነው

    አንድ ወር በሞላው አሜሪካ እና እስራኤል ከኢራን ጋር እያደረጉት ባለው ጦርነት የእስራኤል ጦር ዛሬ አርብ በኢራን ውስጥ በፈጸመው ጥቃት ወሳኝ የአገሪቱን የጦር መሣሪያ ማምረቻ መምታቱን አስታወቀ።

    የእስራኤል አየር ኃይል በፈጸመው ጥቃት የኢራን “ዋነኛ የሚሳዔሎች እና የባሕር ላይ ፈንጂዎች ማምረቻ” ተቋም መመታቱን የአገሪቱ ጦር ገልጿል።

    በማዕከላዊ ኢራን ያዝድ በተባለው ግዛት ውስጥ የሚገኘው ጥቃት የተፈጸመበት ቦታ የአገሪቱ ባሕር ኃይል አብዛኞቹን ሚሳዔሎች እና ባሕር ላይ የሚጠመዱ ፈንጂዎችን የሚያመርትበት መሆኑን እስራኤል አስታውቃለች።

    ኢራን በሺዎች የሚቆጠሩ ባሕር ላይ የሚጠመዱ ፈንጂዎች እንዳላት ይታመናል። ምንም እንኳ እነዚህን ፈንጂዎች በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ አጥምዳቸው ስለመሆኑ ግልጽ ባይሆንም ፈንጂዎቹ በግዙፍ የንግድ መርከቦች ላይ ሊያደርሱ የሚችሉትን ከባድ ጉዳት በመፍራት የመርከቦች እንቅስቃሴ ተገትቷል።

  18. አንድ መኪና እስራኤል ውስጥ በኢራን ሚሳዔል የተመታበትን ቅጽበት የሚያሳይ ቪዲዮ

    ኢራን ለተከፈተባት ጥቃት አጸፋ በእስራኤል እና በሌሎች የመካከለኛው ምሥራቅ አገራት ላይ ያልተቋረጠ የሚሳዔል እና የድሮን ጥቃቶችን እየፈጸመች ነው። አገራቱ ሚሳዔሎችን በፀረ ሚሳዔል ለማክሸፍ እየሞከሩ ቢሆንም በሁሉም ላይ ግን አልተሳካላቸውም።

    በዚህም ሳቢያ በሰው እና በንብረት ላይ ጉዳት እየደረሰባቸው ነው። በዚህ ቪዲዮ ላይ የእስራኤል ሠራዊት ከኢራን የተተኮሰ ነው ያለው ሚሳዔል አንድ መኪና ሲመታ ይታያል።

  19. በእስራኤል የተገደሉት የኢራን አብዮታዊ ዘብ ባሕር ኃይል አዛዥ ማን ናቸው?

    አሊሬዛ ታንግሲሪ

    የፎቶው ባለመብት, Tehran Times

    እስራኤል በሆርሙዝ ባሕር ወሽመጥ ላይ ያለውን አጠቃላይ እገዳ የሚቆጣጠረውን የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ የባሕር ኃይል አዛዥ መግደሏን አስታወቀች።

    የእስራኤል የመከላከያ ሚኒስትር ኢዝራኤል ካትዝ እንዳሉት፣ የኢራን የባሕር ኃይል አዛዥ የሆኑት አሊሬዛ ታንግሲሪ "በቀጥታ የሽብር ተግባር የቦምብ ጥቃት በመፈጸም እና የሆርሙዝ ወሽመጥን በመዝጋት በቀጥታ ተጠያቂ ነበር" ብለዋል። አሁን "ተወግዷል" ሲሉም ተናግረዋል። ሙሉውን ዘገባ እዚህ ያንብቡ እስራኤል ገደልኳቸው ስላለቻቸው የኢራን ባሕር ኃይል አዛዥ ምን ይታወቃል?

  20. ዓለም አቀፉ የአቶሚክ ኤነርጂ የኒውክሌር ተቋማት ጥቃት ከቀጠለ “ትልቅ የራዲዮሎጂ አደጋ” እንደሚከሰት አስጠነቀቀ

    የኒውክሌር ኃይል ማመንጫ ተቋም

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ዓለም አቀፉ የአቶሚክ ኤነርጂ ኤጀንሲ፤ በኢራን የኒውክሌር ተቋማት አቅራቢያ የሚፈጸም ጥቃት የሚቀጥል ከሆነ “ትልቅ የራዲዮሎጂ አደጋ” ያስከትላል ሲል አስጠነቀቀ።

    የተባበሩት መንግሥታቱ ተቋም ማስጠንቀቂያ የሰጠው በኢራን ደቡብ ምዕራባዊ ክፍል የሚገኘው የቡሼራ የኒውክሌር ኃይል ማመንጫ ተቋም አቅራቢያ ማክሰኞ ዕለት በድጋሚ ጥቃት እንደተፈጸመ ከተገለጸ በኋላ ነው።

    የተቋሙ ዋና ዳይሬክተር ራፋኤል ግሮሲ በኢራኑ የኒውክሌር ተቋም አቅራቢያ እየተደጋገመ ያለው “ሰሞነኛው ወታደራዊ ጥቃት እጅግ እንዳሳሰባቸው” ገልጸዋል።

    ዋና ዳይሬክተሩ “ትልቅ ቁጥር ያለው የኒውክሌር ቁስ ይዞ የሚሰራ የኔውክሌር ኃይል ማመንጫ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ፤ በተቋሙ ላይ የሚደርስ ጉዳት ትልቅ የራዲዮሎጂ አደጋ ሊያስከትል እንደሚችል” ማስጠንቀቃቸውን በተቋሙ የኤክስ ገጽ ላይ የወጣው ጽሁፍ ያስረዳል።

    በዚህ ስፍራ የሚከሰት የራዲዮሎጂ አደጋ “ኢራን ውስጥ እና ከዚያም ባሻገር ሰፊ አካባቢን” ሊጎዳ እንደሚችልም ገልጸዋል።

    ይህንን አይነቱን የኒውክሌር አደጋ ስጋት ለማስወገድ ሲባል የጦርነቱ ተፋላሚ አገራት ወታደራዊ እርምጃዎችን ከመውሰድ እንዲቆጠቡ ዋና ዳይሬክተሩ ጠይቀዋል። “በግጭት ወቅት ሰባቱን የኒውክሌር ደኅንነት ማረጋገጫ አምዶች መጠበቅ አስፈላጊ” እንደሆነም አጽንኦት ሰጥተዋል።