እስራኤል የሄዝቦላህ አመራርን ለመግደል በፈጸመችው ጥቃት በስህተት ቡድኑን የሚቃወም ፖለቲከኛ ተገደለ
እስራኤል እሁድ ዕለት በሊባኖስ የሄዝቦላህ አባልን ለመግደል ባደረገችው ሙከራ በስህተት ቡድኑን አጥብቆ የሚቃወም ከፍተኛ የፖለቲካ ቡድን መሪ ተገደለ።
በጉዳይ ላይ የእስራኤል የመከላከያ ሠራዊት ለቢቢሲ በሰጠው ምላሽ ጥቃቱ የታሰበውን ዒላማ መግደል እንዳልቻለ ገልጾ፣ በሲቪሎች ላይ “ለደረሰው ጉዳት መጸጸቱን" ገልጿል።
በአብዛኛው ክርስቲያኖች በሆኑ ግለሰቦች የተዋቀረው የሊባኖስ ኃይሎች ፓርቲ፣ በአንድ የመኖሪያ ሕንጻ ላይ የተፈፀመው ጥቃት የፓርቲውን ከፍተኛ አመራር ፒየር ሞኡዋድን እና ባለቤቱን ፍላቪያን እንደገደለ አስታውቋል።
የመኖሪያ ሕንጻው የሚገኘው ከቤይሩት በስተምሥራቅ በምትገኘው አይን ሳዴህ በምትባል በአብዛኛው የክርስትና እምነት ተከታዮች መኖሪያ በሆነችው ከተማ ውስጥ ነው።
የሊባኖስ የጤና ሚኒስቴር ጥቃቱ አንድ ወንድ እና ሁለት ሴቶችን እንደገደለ አስታውቋል።
የአካባቢው ከንቲባ ሟቾቹ ይኖሩ የነበረው ከዒላማው በታች ባለ አንድ ፎቅ ውስጥ ነበር ብለዋል።
የእስራኤል መከላከያ ሠራዊት "በርካታ የማይመለከታቸው ግለሰቦች በጥቃቱ ምክንያት ጉዳት እንደደረሰባቸው መመልከት ችለናል" ብሏል።
የሊባኖስ ኃይሎች ፓርቲ ፒየር ሞአዋድ "ተዋጊም ሆነ ወታደራዊ ዒላማ አልነበረም" ካለ በኋላ ከአሰቃቂው ጥቃት በፊት ከቤተሰቡ ጋር የትንሳዔ በዓልን እያከበረ እንደነበር ተናግሯል።
ፓርቲው ሄዝቦላህን አውግዞ ጥቃቱ የተከሰተው ወታደራዊ ግጭቶች ወደ መኖሪያ መንደሮች ዘልቀው እየመጡ በመሆናቸው ነው ብሏል።