ኢራን በሳዑዲ በፈጸመችው ጥቃት የአሜሪካ ወደታራዊ ጄት መመታቱ ተረገጋጠ
ሳዑዲ አረቢያ ውስጥ በሚገኝ የአየር ኃይል ሰፈር ላይ በተፈጸመ ጥቃት የአሜሪካ የወደታራዊ ማዘዣ እና መቆጣጠሪያ አውሮፕላን መመታቱን ትክክለኛነታቸው የተረጋገጡ ፎቶዎች አመለከቱ።
ከሳምንታት በፊት የተፈጸመውን ጥቃት የሚያሳዩ ፎቶዎች መጀመሪያ ላይ የተጋሩት የአሜሪካ ወታደራዊ ዜናዎችን በሚያወጣው የፌስቡክ ገጽ ላይ ነበር። ምሥሎቹ ኢ-3 ሴንትሪ የተባለው አውሮፕላን ለሁለት ተገምሶ አሳይተዋል።
ቢቢሲ ባደረገው ማጣራት ፎቶዎቹ ከሳዑዲ ዋና ከተማ ሪያድ ደቡብ ምሥራቅ 100 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በሚገኘው የልዑል ሱልጣን አየር ኃይል ሰፈር የተነሱ ናቸው። በአውሮፕላኑ ዙሪያ የሚታዩት ነገሮች ከሳተላይት ምሥሎች ጋር ተመሳሳይ ናቸው።
የቢቢሲ የመረጃ ማጣሪያ ቢቢሲ ቬሪፋይ ከጥቃቱ ቀን በፊት የወደመው ኢ-3 አውሮፕላን በስፍራው እንደነበረ በሳተላይት ምሥል የተመለከተ ሲሆን፣ ጉዳቱ የደረሰበት ተመሳሳይ አውሮፕላን ነው ለማለት ግን እርግጠኛ አይደለም።
ማጣራት ከተደረገባቸው ፎቶዎች መካከል በአንዱ ላይ የአውሮፕላኑ የጭራ ቁጥር ይታያል። ቁጥሩን በመጠቀም በተደረገው ማጣራት አውሮፕላኑ በበረራ ላይ እንደነበር ለማረጋገጥ ተችሏል።
በጥቃቱ ዕለት የተወሰዱ የሳተላይት ምሥሎች በአየር ኃይል ሰፈሩ ውስጥ እሳት እንደነበር አሳይተዋል። ነገር ግን እሳቱ ኢ-3 አውሮፕላኑ ላይ ጉዳት በደረሰበት ጥቃት የተነሳ ስለመሆኑ ግልጽ አይደለም።
ከጥቃቱ በኋላ አንድ የአሜሪካ ባለሥልጣን ለሮይተርስ ዜና ወኪል ኢራን በአየር ኃይል ሰፈሩ ላይ በፈጸመችው ጥቃት ሁለት በጽኑ የቆሰሉትን ጨምሮ 12 የአሜሪካ ወደታሮች መጎዳታቸውን ተናግሮ ነበር።